fredag 21. august 2015

ወጣቶቹን እየበላ ያለው ስርዓት … (ግርማ ሠይፉ ማሩ)

ግርማ ሠይፉ ማሩ
  • 116
     
    Share
ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ በቀጣይ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ የተመረጡ እና የተለመዱ ፊቶችን ስብስበው ጥያቄ ሲያቀርቡና ማብራሪያ ሲሰጡ ነበር፡፡ የእኔን ቀልብ የሳበው ግን አውቀውም ይሁን ሳያውቁት ወጣቶችን እየበላ ያለ ስርዓት ባለቤት እና መሪ መሆናቸውን የገለፁበት አስተያየት ከታዳሚው ሞቅ ባለ በተደጋጋሚ ጭብጨባ መታጀቡ ነው፡፡ ባለፈው የኦባማ ጉብኝት ወቅት ዲሞክራሲ ማላት ምርጫ በስላም ማጠናቃቅ ብቻ አይደለም፡፡ ጋዜጠኞችን አክቲቪሰቶችን እስር ቤት እያወረዱ አማራጭ ፖለቲካን እየከለከሉ ዲሞክራሲ የተሟላ አይሆኑም ብለው ሲሞልጯቸው በጭብጨባ ያጅቡ ነበር፡፡ ዛሬም ተመሳሳይ ነገር ነው የሆነብኝ፡፡
ይህን ፅሁፍ ከመለጠፌ በፊት ግን በእስር ላይ ያሉ ጓዶቻችን ከእስር እንዲፈቱ ፍርድ ቤት መበየኑን ሰምቻለሁ፡፡ ንፁህ ናችሁ ብሎዋቸዋል፡፡ ንፁህ ነበሩ እና አይገርምም፡፡ ይህን ማበረታታት አለብን፡፡ እነ አንዱዓለም፣ ናትናኤል፣ እስክንድር፣ ተመስገን ደሳለኝ ፣ ወዘተ መለቀቅ አለባቸው፡፡ ይህን ጥሩ እርምጃ ኦባማ ተቆጥቷቸው ነው እያሉ ከማንቋሸሽ ይህን እያጣጣምን ተጨማሪ መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ለማነኛውም ለቤተሰቦች ዕዳ ሆነው የነበሩት ታጋዮች ነፃ ወጥተዋል፡፡ ከቂሊንጦ!!! እንኳን ደስ ያላችሁ ደስ ያለን!!!
ወደ ተነሳሁብ ነጥብ ሰመለስ ጠቅላይ ሚንስትሩ ጉቦ የሚበላባቸው መስሪያ ቤቶች እንዳሉ ማወቅ ብቻ አይደለም ወጣቶችንም ጉበኛ አድርጎ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አስልጥኖ ወደ ተግባር እንደሚያስገባ በግልፅ ነግረውናል፡፡ በተጨማሪ ምንም ዓይነት የተሟላ ማስረጃ ቢኖረን ጉዳያችንን መጨረስ የማንችልባቸው የመንግስት ተቋማት እንዳሉም ጠቅላይ ሚኒስትራችን ጠንቅቀው ያውቃሉ እነዚህም ተቋሞች የሰለጠኑ አዲስ ምሩቃን ወጣቶች ስራ እንዲሰሩ ሲመደቡላቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዴት ጉዳይ ማለቅ እንደሌለበት ጠንቅቀው ይማራሉ፡፡ ይህንንም በተግባር ይፈፅሙታል፡፡ እነዚህ መስሪያ ቤቶች የመንግስት አገልግሎት መስጫ ነው፡፡
ባለጉዳይን በአግባቡ እና በስርዓት ያለማስተናገድ በእርሰቸው ቃል አመናጫቂና አንጓጣጭ መስሪያ ቤቶችም እንዲሁ የተመደቡላቸውን ወጣት ምሩቃን በፍጥነት ቀይረው ተገዶ አገልግሎት ፍለጋ የመጣውን ተገልጋይ ያመናጭቃሉ፣ ይሳደባሉ፡፡ ይህን ስስማ የጤና ባለሞያዎቻችን ወላዶችን በምጥ ወቅት ማን አርግዥ አለሽ አትጩሂ ሲሉ ተሰማኝ፡፡ ሌሎች የሚሉትን ፀያፍ ቃል ለዚህ ፅሁፍ ስለማይመጥን ዘልየው ነው፡፡
የሀገር ውስጥ ገቢ ኦዲተሮች እና ገማቾች በግብር ከፋይ ዜጎች ላይ ያላቸውን “ቬቶ ፓውር” ማወቅ ብቻ አይደለም፣ ጠቅላይ ሚኒስትረ ተሰፋ የቆረጡበት ሁኔታ ያለ የሚመስል አስተያየት ነው የሰጡት፡፡ ሂሳብ ሰርታችሁ ካልመጣችሁ እንደፈለጉ ያድርጓችሁ የሚሉን ይመስላል፡፡ ለአፋቸው እንኳን እነዚህን ልክ ማስገባት አለብን የሚል ተሰፋ አልሰጡንም፡፡ እኔ በግሌ የሀገር ውስጥ ኦዲተር ብሆን ስራ አቆም ነበር፡፡ ደግነቱ እግዜር አንድኖኛል፡፡ በእኛ ሀገር መስሪያ ቤቱ ሲሰደብበት ኃላፊነቱን የሚለቅ ባለስልጣን ስለሌለን ነው፡፡ እራሴ እለቅ ነበር ያልኩት፡፡
እነዚህን ሁሉ ወጣቶችን የሚበሉ መስሪያ ቤቶች የሚተዳደሩት በመንግሰት በጀት፣ በምርጫ አሸንፌ ስልጣን ያዝኩ በሚል መንግሰት በሚሾሙ የፖለቲካ ሾመኞች መሆኑን የዘነጉት ይመስላሉ፡፡ ይህን ለማለት ያስቻለኝ ደግሞ መፍትሄው የታጋይ ዜጋ መኖርና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ነው በማለት አስቀምጠው፣ የፖለቲካ ቁርጠኝነት በተመለከት ጠንካራ ፓርቲና አመራር በመኖሩ ተገባራዊ ማድረግ ይቻላል በሚል አሹፈውብናል፡፡
ይህን ፕሮግራመ የተከታተልን ሰዎች ታጋይ ዜጎችን በእኔ ትርጉም እንቢ ሙሰኝነት ….. ያሉትን፣ የመልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የጮሁትን እና የዘመሩትን፣ መንግሰት ይህን ጉዳይ የማያውቅ ከሆነም እንዲገባው የጦመሩትን፣ የፖለቲካ ሙሰኝነት እንዲቀር እንቅልፉን አጥቶ ጋዜጣና መፅሄት በማዘጋጀት የሚተጉትን ጋዜጠኞችን እስር ቤት እያጎሩ እንዴት ታጋይ ዜጋ እንደሚፈራ አልታይህ አለኝ፡፡
ታጋይ ዜጋ እንዳይፈራ ዜጎችን አንገት እያስደፉ ፖለቲከኞች በሚፈነጩበት ሀገር ኪራይ ስብሳቢነት አንገቱን እንዴት እንደሚደፋ ማወቅ አይቻልም፡፡ ታጋዮችን አንገት አስደፍቶ ሌቦች ፖለቲከኞችን ቁርጠኞች ናቸው ማለት ፌዝ ነው፡፡
ታጋይ ዜጋ እናፍራ – ታጋይ የሆነ ዜጋ ጉቦ አይከፍልም በዚህ ጊዜ ኪራይ ስብሳቢነት ይደፈቃል ነው ብለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነገር ግን ጉቦ አልሰጥም የሚል ዜጋ ለማፍራት፣ ከፖለቲከና ዱላ የሚጠብቅ ሲቪል ማህበረሰብ፣ ጋዜጠኛ የግድ ይለናል፡፡ ፍርድ ቤት ያስፈልገናል፡፡ ያስቸገሩንን ወሰደን የምንገትርበት፡፡ የመርጊያ በቃናን ውሳኔ የሚያፀና ፍርድ ቤት አለን ብለን ጉቦ አንከፍልም በሉ ብለን እዝቡን ለጅብ አንሰጥም፡፡ መልዕክቴ ስርዓቱ ከፖለቲካ ሙሰና ከፀዳ እርገጠኛ ይሁኑ ሌሎች ሙስናዎች ተራ ናቸው፡፡ ለማነኛውም ይህ ወጣቶችን እየበላ ያለው የፖለቲካ ስርዓት ይገራልን፡፡
ቸር ወሬ ያሰማን!!!!! ዛሬ ደስ ብሎኛል ደስ ይበላችሁ!!!!
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9727#sthash.PyNQLVuH.dpuf

torsdag 20. august 2015

በፍትህ እንዲህ የተቀለደበት ዘመን ይኖር ይሆን?

ከፋሲል የኔዓለም
(የኢሳት ጋዜጠኛ)
ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም
ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም
ወንድሞቼ ዳንኤል፣ አብርሃም፣ የሽዋስና ሃብታሙ ይፈታሉ በመባሉ በጣም ደስ ብሎኛል። በመፈታታቸው ደስ እየተሰኝን የአገዛዙን ፖለቲካዊ ጨዋታ ማየቱም አይከፋም። ከዚህ ቀድም እንዳልኩት ነው፤ አገዛዙ እድሜውን የሚያራዝመው በሰላማዊ ትግል እና በትጥቅ ትግል መካከል ያለውን የሃሳብ ልዩነት በማራገብ ነው። ሰላማዊ ትግልን የሚያቀነቅኑ ሃይሎች እየጠነከሩ ሲመጡ፣ የትግሉን መሪዎች ያስርና ህዝቡ “ሰላማዊ ትግል አያዋጣንም” ብሎ ወደ ትጥቅ ትግል ፊቱን እንዲያዞር አድርጎ አደጋውን ይቀንሰዋል። የህዝቡ ትኩረት ወደ ትጥቅ ትግል ሲዞር ደግሞ፣ የታሰሩ ሰላማዊ ታጋዮችን ይፈታና የፖለቲካ ምህዳሩንም ትንሽ ከፈት አድርጎ ” አዲስ የተስፋ ዳቦ” ይሰቅላል ። ህዝቡም እንደገና በሰላማዊ ትግል ተስፋ ያደርግና ትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ልቡ ያመነታል- የታጋዩን ልብ እየከፋፈሉ የመግዛት ፖለቲካ ። የእነ አብርሃን መፈታት “ሃሳብን ከፋፍሎ በመግዛት የፖለቲካ ስልት ” ካየነው ስሜት ይሰጣል።
የተፈቱትም ሆነ ለወደፊቱ የሚፈቱት ታጋዮች ቆራጥ የሰላማዊ ትግል አቀንቃኞች ናቸው፤ ከመጀመሪያውም የታሰሩት ሰላማዊ ትግሉ በምርጫው ላይ ተጽኖ እንደሚፈጥር ስለታወቀ ነው። ከምርጫው በሁዋላ፣ በተለይም ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ጓዙን ጠቅልሎ የትጥቅ ትግል ወደሚደረግበት በረሃ ሲወርድ፣ ህዝባዊ ንቅናቄው በከፍተኛ ደረጃ አድጓል። ይህን ህዝባዊ ንቅናቄ ለመቀልበስ አገዛዙ ፣ ሰላማዊ ታጋዮችን በመፍታትና የፖለቲካ ምህዳሩን ትንሽ ገርበብ በማድረግ የህዝቡን ልብ ለመከፋፈል የተለመደ ስልቱን ተግባራዊ ለማድረግ አቅዷል። ይህ ስትራቴጂ የተበላ እቁብ በመሆኑ ከእንግዲህ ውጤት ያመጣል ብሎ መጠበቅ የዋህነት ነው። አንደኛው የትግል አማራጭ ( የትጥቅ ትግሉ) ጉልምስና እድሜ ላይ ደርሷል፤ አገራችን በውጭ ስትወረር ካልሆነ በስተቀር ህዝቡ በዚህ ደረጃ ተነቃንቆ ትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ፍላጎት ሲያሳይ ስመለከት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ” ትግሉን መቀላቀል እንፈልጋለን” እየተባለ ከአገር ቤት በየቀኑ የሚደወለው ስልክ አስገራሚ ነው፤ እንዲያውም ስልክ የምታነሳው ባልደረባዬ ” የኢትዮጵያ ህዝብ በመሉ ጫካ ከገባ ነጻ አውጪዎች ነጻ የሚያወጡት ማንን ነው? በማለት በጣም ተገርማ ጠይቃኛለች ። ከአገር ቤት ስለሚደወሉ ስልኮች ደግሞ አገዛዙ በቂ መረጃ አለው፤ የህዝቡንም ስሜት ያውቀዋል። ይህን የተባለበትን ቁማር እንደገና ለመቆመር የተነሳውም ለዚህ ነው። እኔ ሁለቱም የትግል ስልቶች በስልት ከተካሄዱ ተደጋጋፊ ናቸው ብዬ አምናለሁ። ስርዓቱን በውስጥም በውጭም በመወጠር፣ ልክ እሱ የታጋዮችን የትኩረት አቅጣጫ በመከፋፈል የነጻነት ትግሉን ለማዳከም እንደሚሞክረው ሁሉ፣ ታጋዮችም በተመሳሳይ ስልት የእሱን የትኩረት አቅጠጫ በማሳት ሊያዳክሙት ይችላሉ። የእነ ዳንኤል መፈታት ትግሉን ወደፊት ይገፋዋል እንጅ አያዳክመውም።
habitamu
እግረ-መንገዴን ስለሚያብከነክነኝ አንድ ነገር ትንሽ ልበል። ሃሳቡን ዮና ብር የተባለ ጎበዝ ጸሃፊ አንስቶት አይቻለሁ ። እንደሚታወቀው በዘፈቀደ እየታፈሱ የሚታሰሩና የሚፈቱ የአገሬ ብርቅዬ ልጆች ይቅርታም ካሳም ተከፍሏቸው አያውቅም። ዘመዶቻቸው እነሱን ለመጠየቅ ሲመላለሱ የገንዘብ ፣ የጊዜና የጉልበት ኪሳራ አጋጥሟቸዋል። ልጆቻቸው የወላጆቻቸውን ፍቅር እንዳያገኙ በመከልከላቸው በአእምሮ እድገታቸው እና በወደፊቱ ህይወታቸውም ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተጽኖ ይፈጠርባቸዋል። ስራ መስራት ባለመቻላቸው የኑሮ ቀውስ ያጋጥማቸዋል። ሽብርተኛ በመባላቸውም የሞራል ኪሳራ ይደርስባቸዋል። የግል ህይወቴን የተመለከቱ ጉዳዮችን ማንሳት ባልፈልግም፣ ለዚህ ውይይት ስለሚጠቅም ለዛሬ አንድ ነገር አነሳለሁ። ከ5 ዓመታት በፊት፣ ወደ ሆላንድ ከመጣሁ በሁለተኛው አመት፣ የገጠመኝ አንድ ትልቅ ችግር ነበር። ኢሳት እንደተቋቋመ፣ እንደዛሬው በቂ የሰው ሃይል ሳይኖርና በየአገሩ ስቱዲዮዎች ሳይመሰረቱ፣ የሆኑ ሃይሎች “ኢሳትን ማስቆም አለብን” ብለው ተነሱና በእኔ ላይ ክስ መሰረቱ። እነዚህ እኩይ ሰዎች፣ ” ህገወጥ የገንዘብ ዝውውር ይሰራል፤ ህገወጥ ገንዘብ ያገኛል፣ ሰዎችን በህገወጥ መንገድ ወደ አውሮፓ ያስገባል ወዘተ” የሚል ደብዳቤ ጽፈው ለፖሊስ አስገቡ። የተጠቀሱት ወንጀሎች በጣም አደገኛና ከአገር የሚያስባርሩ ወይም የሚያሳስሩ ናቸው። ያው ጥቆማ ቀርቧልና ፖሊስም ምርመራ ጀመረ። ሁለት ጊዜ ተጠርቼ ተጠየኩ፤ መርማሪዎች ቤታችን ድረስ መጥተው አኗኗራችንን አዩት። የባንክ አካውንቴ ተመረመረ፣ ስለኢሳት አጀማመርና የገንዘብ ምንጭ ሳይቀር ተጠየቀኩ፣ የሁዋላ ታሪኬ ሁሉ ተመረመረ። የመንግስት ክፍያም ለሁለት ወራት በግማሽ ቀነሰ። ሰዎች መከሩኝና በነጻ ጠበቃ ወደሚያቆም ድርጅት ሄድኩ። በሳምንቱ፣ ከጠበቃዬ ጋር ፍርድ ቤት ቀረብኩ። ፍርድ ቤቱ ፋይሉን አገላብጦ እንደቆምኩ ውሳኔ ሰጠ። “በአጉል ጥርጣሬ ለተደረገው ምርምራ የይቅርታ ደብዳቤ ይጻፍ፣ ለቃለምልልስ በሚል ሁለት ቀናት ስራ በመፍታቴ ክፍያ ይከፈለው፣ የታገደው የሁለት ወር ክፍያ ይለቀቅለት እንዲሁም በእሱና በቤተሰቡ ላይ ለደረሰው የሞራል ካሳ መዘጋጃው በመስፈርቱ መሰረት ይክፈለው” አለ። አጠቃላይ የገንዘብ መጠኑ ተስልቶ እንደሚነገረኝ፤ በክፍያው ላይ ቅሬታ ካለኝመ ይግባኝ እንድል፣ ስራዬን እንደሚያደንቁ አበረታተው አሰናበቱኝ። በፍጹም ማመን አልቻልኩም። ከቀናት በሁዋላ የይቅርታ እና የገንዘብ ዝርዝር የያዘ ወፍራም ደብዳቤ ደረሰኝ። ጠበቃው ” ገንዘብ አንሶኛል የምትል ከሆነ ይግባኝ እጠይቃለሁ” አለኝ። (እሱም ራሱ ለአንድ ቀን ፍርድ ቤት ስለቀረበ ብቻ ጠቀም ያለ ክፍያ አግኝቷል። ) አይሆንም አልኩት።
የ97ቱን ምርጫ ተከትሎ ከሌሎች ጋደኞቼ ጋር ለአንድ አመት ከ ስምንት ወር ያክል ጊዜ ታስሬ በነጻ ተለቅቄያለሁ። በታሰርኩባቸው ወራት ስራ ብሰራ ኖሮ ላገኝ የምችለውን ገንዘብ እንርሳውና በተለያዩ ምክንያቶች ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ ኪሳራ ደርሶብኛል። ባለንብረት የነበርኩ ሰው ንብረት አልባ ሆኜ ተፈትቻለሁ፤ ለዚህ ሁሉ ግን ካሳ ሊከፈለኝ ቀርቶ የተወሰደብኝ ኮምፒዩተር እንኳ አልተመለሰልኝም፤ ስጠይቃቸው ” ገና መቼ ተነካህና ነው” ብለው አሰናብተውኛል። በሰው አገር ለሁለት ቀናት ተጠርቼ በመጠየቄ ብቻ ጠቀም ያለ የሞራል ካሳ ክፍያ ሲከፈለኝ፣ በአገሬ ለረጅም ጊዜ ታስሬ ስፈታ፣ የሞራል ካሳ ሊከፈለኝ ቀርቶ የተወሰደብኝ ንብረት እንኳ በወጉ አልተመለሰልኝም። ልብ በሉ! ለአንድ ቀን ታስሬ ብፈታ ኖሮ የሚሰጠኝ የሞራል ካሳ በዚያው ልክ ይጨምር ነበር። እነርዕዮት፣ የሽዋስ፣ ሃብታሙና ሌሎችም በግፍ የታሰሩት ወገኖቻችን ሁሉ ፍትህ የሚያገኙበት ቀን እሩቅ ባለመሆኑ እንጽናናለን እንጅ፣ የደረሰው ጉዳትስ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም።
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/46066#sthash.9DvL7SmP.dpuf

“በደረሰብኝ በደል ወደ አርበኞች ግንባር ገብቻለሁ” – የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበሩ ተጠርጣሪዎች

ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው
  • 330
     
    Share
ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው
ሰላማዊ ትግል የማያዋጣ በመሆኑ ከግንቦት ሰባትና አርበኞች ግንባር ጋር በመቀላቀል መንግሥትን በትጥቅ ትግል መገልበጥ እንዳለባቸው በማመን ወደ ኤርትራ ሊሻገሩ ሲሉ፣ የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለዋል የተባሉት የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበሩ አራት ተጠርጣሪዎች፣ ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል እየሄዱ እንደነበር ለፍርድ ቤት የእምነት ቃላቸውን ሰጡ፡፡
በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ የተለያየ ኃላፊነት የነበራቸው ተከሳሾቹ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ እየሩሳሌም ተስፋ፣ ፍቅረማርያም አስማማውና የአርበኞች ግንባር አባል መሆኑን የገለጸው ደሴ ካሳዬ ሲሆኑ፣ የእምነት ክህደት ቃላቸውን የሰጡት ጉዳዩን እየመረመረው ለሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ነው፡፡
ሁሉም ተከሳሾች ድርጊቱን መፈጸማቸውን ነገር ግን ጥፋተኛ አለመሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ ብርሃኑ ለፍርድ ቤቱ እንደተናገረው፣ ‹‹አገሬ ጨቋኝ ሥርዓት ውስጥ ስላለች ይኼንን ለመታገል ግንቦት ሰባት ከተባለ ነፃ አውጭ ድርጅት ጋር ለመገናኘት ጉዞ ጀምሬያለሁ፡፡ ስለዚህ ድርጊቱን ፈጽሜያለሁ፡፡ ግን ጥፋተኛ አይደለሁም፤›› ብሏል፡፡
ኢየሩሳሌምም ድርጊቱን መፈጸሟን አምና ጥፋተኛ አለመሆኗን ገልጻለች፡፡ ሦስተኛው ተከሳሽ ፍቅረ ማርያም ደግሞ ዴሞክራሲ ለማስፈን ድርጊቱን መፈጸሙን ገልጾ፣ ጥፋተኛ አለመሆኑን አስረድቷል፡፡
ትግሪኛ እንጂ አማርኛ እንደማይሰማ የገለጸው አራተኛ ተከሳሽ ችሎቱ አስተርጓሚ እንዲቀርብለት ካደረገ በኋላ በሰጠው የእምነት ቃል፣ ‹‹በደረሰብኝ በደል ወደ አርበኞች ግንባር ገብቻለሁ፡፡ ድርጊቱን ፈጽሜያለሁ፡፡ ነገር ግን ጥፋተኛ አይደለሁም፤›› በማለት የእምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ ተከሳሾቹ ድርጊቱን መፈጸማቸውን አምነው ጥፋተኛ እንዳልሆኑ በመግለጽ በመቃወማቸው ምክንያት፣ ዓቃቤ ሕግ ጥፋተኛ ስለመሆናቸው የሚያስረዱለትን ምስክሮች ነሐሴ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. አቅርቦ እንዲያሰማ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
Source:: Ethiopian Reporter
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9696#sthash.mZzJmW7B.dpuf

onsdag 19. august 2015

በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል የጅምላ ግድያ በመንግስት ሃይሎች እየተፈጸመ ነው ተባለ

0
  • 154
     
    Share
በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል መንጌ ወረዳ የመንግስት ሃይሎች አርብ እለት በሰነዘሩት ጥቃት 12 ሰዎች ተገደሉ። ከሟቾቹ ውስጥ 5ቱ ህይወታቸው ያለፈው እስር ቤት ከተወሰዱ በኋላ በምግብ ተመርዘው እንደሆነ የቤኒሻንጉል ህዝቦች ነጻነት ንቅናቄ አስታወቀ።
የቤኒሻንጉል ህዝቦች ነጻነት ንቅናቄ (ቤሕነን) ሊቀመመንበር አቶ አብዱልዋህድ መሃዲ ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደገለጹት አርብ ነሐሴ 8 ቀን 2007 የመንጌ ወረዳ ነዋሪዎች በስርዓቱ ላይ ያላቸውን ምሬት በሰላማዊ ሰልፍ የገለጹ ሲሆን፣ በአካባቢው ተሰማርቶ የሚገኘው የፌዴራል ፖሊስ በከፈተው ተኩስ 12 ሰዎች ሲገደሉ፣ 56 ሰዎች ቆስለዋል። 5ቱ ደግሞ በእስር ቤት ተመርዘው ሞተዋል።
ከሟቾቹ ውስጥ አባትና ልጅ እንዲሁም ወንድማማቾች እንደሚገኙበት አቶ አብዱልዋህድ መሃዲ በዝርዝር ገልጸዋል።
ህዝብ ላይ በሚደረገው የሃይል እርምጃ በቅርቡ በተካሄደው ምርጫ ወቅትም መታየቱን የገለጹት የቤሕነን ሊቀመንበር አቶ አብዱልዋህድ መሃዲ፣ በወቅቱ 2 ሰዎች መገደላቸውን፣ የራሳቸውን አባት ጨምሮ በርካታ አዛውንቶች የተካተቱበት 54 ሰዎች መታሰራቸውንን ገልጸዋል።
80 አመት ያለፋቸው የእርሳቸው አባት ጨምሮ ለ 54ቱ ሰዎች መታሰርና አሁንም ድረስ በእስር ቤት መቆየት ምክንያት የሆነው በምርጫ ወቅት ህዝብ የክልሉን ገዢ ፓርቲ እንዳይመርጥና በምርጫው እንዳይሳተፍ ተሳትፋችኋል የሚል እንደሆነም ተመልክቷል።
አርብ እለት የተካሄደው ግድያ የዚያ ቀጣይ እንደሆነ የገለጹት የቤሕነን ሊቀመንበር፣ የተጠቀሰው የሟቾች ቁጥር የታወቀውና በስም የተረጋገጠው እንጂ ከዚያ የበለጠ ሰው ሊሞት እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸዋል።
የቆሰሉት 56 ሰዎች በመንጌ ወረዳ በአሶሳ ሆስፒታል በህክምና ላይ መሆናቸውን ለኢሳት ገልጸዋል።
በቤኒሻንጉል ክልል መንጌ ወረዳ የተፈጸመውን ግድያ በተመለከተ የአካባቢው ምንጮች ለኢሳት ያረጋገጡ ሲሆን በመንግስት ወገን የተሰጠ ማስተባበያ የለም

- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9658#sthash.pqUPiyM4.dpuf

tirsdag 18. august 2015

የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ እድር ላይ ጥያቄ አነሳህ ተብለው ታሰሩ




(ነገረ ኢትዮጵያ) በባሌ ዞን ሰልጣ ቀበሌ፣ ሲናና ወረዳ የሰማያዊ ፓርቲ የፓርላማ ዕጩ ተወዳዳሪ የነበሩት አቶ ወርቅነህ ጋድይ አያና የእድር ስብሰባ ላይ ጥያቄ ጠይቀሃል ተብለው መታሰራቸውን የሰማያዊ ፓርቲ የዞኑ አስተባባ አቶ ደመላሽ በቀለ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ በተለይ ከምርጫው በኋላ ካድሬዎች አቶ ወርቅነህ እድርን ጨምሮ ከማህበራዊ ጉዳዮች እንዳይሳተፉ ጫና ሲያደርጉባቸው እንደነበረም ተጠቅሷል፡፡ ሆኖም የአካባቢው ህዝብ ‹‹በፖለቲካ መሳተፍ ህገ መንግስታዊ መብቱ ነው፡፡ እድር ደግሞ ማህበራዊ መብቱ በመሆኑ መሳተፍ አለበት›› በማለቱ እስካሁንም የእድር አባል ሆነው ቢቀጥሉም በእድሩ አካሄድ ጥያቄ አለኝ በማለታቸው ‹‹ለምን ጥያቄ ትጠይቃለህ?›› ተብለው እንደታሰሩ አስባባሪው ገልፀዋል፡፡ አቶ ወርቅነህ ጋድይ በአሁኑ ወቅት በሲናና ወረዳ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል የአስተዳደር አካላት የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ላይ በሚፈፅሙት በደል ምክንያት ከትግል ውጭ ፍትህ እናገኛለን ብለው እንደማያምኑ አቶ ደመላሽ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/45975#sthash.ZMf5WjA5.dpuf

onsdag 12. august 2015

አለቃዎ ሳይሆን ቅን ህሊናዎ የሚያዝዎትን በመፈፀም መልካም ዜጋ ይሁኑ!

August 12, 2015
def-thumbመልካም ዜጋ ማለት ምን ማለት ነው?
ይህን ጥያቄ ለመመለስ በርካታ መጻሕፍት መፃፍ ይቻላል፤ መሠረተ ሀሳቡን ግን በጥቂት ዓረፍተ ነገሮች ማቅረብ ይቻላል።
መልካም ዜጋ ኢፍትሃዊ ተግባር ሲፈፀም “እኔ ምናገባኝ?” አይልም። መልካም ዜጋ “ያባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ”፤ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶም አይብቀል”፤ “እያለህ ካልሆነ ከሌለህ የለህም” እና በርካታ መሰል ምሳሌዎችን አይሰማም። መልካም ዜጋ በማናቸውም ሁኔታ ውስጥ ቢሆን ከነፃና ቅን ህሊናው ጋር ታርቆ ይኖራል።
የህወሓት አገዛዝ፣ መልካም ዜጋ ማለት የመንግሥት ሥልጣን የያዘን ማንኛውም አካል ማክበርና በታማኝነት ማገልገል ተደርጎ እንዲተረጎምለት ይሻል። ፍትህ የሚያዛባ መንግሥትን መቃወም የመልካም ዜጋ አቢይ ተግባር መሆኑ የዘመናችን ወጣት እንዳይገነዘብ ያደርጋል። በተለይ ባለሙያዎች የሚያገለግሉትን አገዛዝ ባህርይ እግምት ውስጥ ሳያስገቡ የተቀጠሩበትን ሥርዓት በታማኝነት ማገልገል የዜግነት ግዴታቸው አድርገው እንዲወስዱት ይወተውታል።
ኦስካር ግሮኒንግ ( Oskar Groening)የዘጠና አራት ዓመት ሽማግሌ ጀርመናዊ ነው። በጀርመን የሂትለር አገዛዝ ወቅት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ንፁሃን የተፈጁበት አሽዊትስ ካምፕ ውስጥ የሂሳብና ጽህፈት ሠራተኛ ነበር። ኦስካር ግሮኒንግ አንድም ሰው አልገደለም፤ አንድም ሰው አልገረፈም። እሱ ሂሳብ ነው የሠራው። ሆኖም በደል ሲፈፀም አይቶ “ምናገባኝ” ብሎ አልፏልና ከብዙ ዓመታት በኋላ ተከሶ በቅርቡ የ4 ዓመታት እስር ተፈርዶበት በሁለት እግሮቹ መቆም በማይችልበት በ 94 ዓመቱ በእርጅናውና በመጦሪያው ዘመን ቤተሰቦቹና ጓደኞቹ ፊት ተዋርዶ እስር ቤት ወርዷል።
በአንፃሩ ኦስካር ሽንድለር (Oskar Schindler) በጀርመን ናዚ ወቅት ሂትለር ይመራው የነበረው የናዚ ፓርቲ አባልና ሰላይ ነበር። ሆኖም ግን የሥርዓቱን ኢሰብዓዊነት ሲረዳ እዚያው የናዚ ፓርቲ ውስጥ ሆኖ አለቆቹ ያዘዙትን ሳይሆን ቅን ህሊናው ያዘዘውን በምስጢር መሥራት ጀመረ፤ በዚህም የ 1200 ሰዎችን ሕይወት ታደገ። ከጦርነቱ በኋላ ኦስካር ተከብሮ የኖረ በርካታ የክብር ስሞችና ሽልማቶች የተሰጠው በመልካም አርዓያነቱ የሚጠቀስ ሰው ሆነ።
በአገራችንም በአምስት ዓመታቱ የፋሽስት ወረራ ወቅት ስመ ጥር የውስጥ አርበኞች ነበሩ። ከነፃነት በኋላ ባንዶች እንኳን በውስጥ አርበኝነት ለመጠራት ያደርጉት የነበረውን እሽቅድድም ልብ በሉ።
በህወሓት፣ ብአዴን፣ ኦህዴግ፣ ደህዴግ እንዲሁም አብዴፓ፣ ቤጉህዴፓ፣ ጋህአዴን፣ ሀብሊና ኢሶዴፓ ያላችሁ ወገኞች ኦስካር ግሮኒንግን ወይንስ ኦስካር ሽንድለርን መምሰል ትፈልጋላችሁ? በህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት ውስጥ ያላችሁ ወገኖቻችን ነገ የምትዋረዱበትን ሥራ መሥራት ነው የሚበጃችሁ ወይስ ዛሬ ከህሊናችሁ ጋር ታርቃችሁ እየኖራችሁ ነገ ደግሞ ልጆቻችሁና የልጅ ልጆቻችሁ የሚኮሩበትን ተግባር መፈፀም ትፈልጋላችሁ? በአገዛዙ የስለላ ድርጅቶች ውስጥ ያላችሁ ወገኖች ስማችሁን በመልካም ማስጠራት አትሹምን?
ልቦና ያላችሁ ወገኖቻችን ሆይ! መልካም ዜግነት ሎሌነት አይደለም። መልካም ዜግነት ለቅን ህሊና ታማኝ መሆን ነው። መልካም ዜግነት ሲመች በገሀድ፤ ሳይመች በምስጢር ኢፍትሃዊነትን መዋጋት ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ በማናቸውም መንገድ በአገዛዙ የፓለቲካ፣ የጦርና የፓሊስ ተቋማት፤ በስለላም ይሁን በሌላ የሲቪል ሙያ የተሰማራችሁ ወገኖቻችን የታዘዛችሁትን ሳይሆን ቅን ህሊናችሁ የሚጠይቃችሁን በመሥራት ኢፍትሃዊ፣ ፋሽስታዊና ዘረኛ የሆነውን የህወሓት አገዛዝን እንድታዳክሙ ጥሪ ያቀርብላችኋል። በአገዛዙ ውስጥ ሆናችሁ እያለም የምትሠሩት ለሀገርና ለትውልድ የሚጠቅም በርካታ ሥራ አለ። የአገዛዙን ምስጢራዊ ሰነዶች ለአርበኞች ግንቦት 7 እንዲደርስ ማድረግ፤ አሊያም በማኅበራዊ ሚዲያዎች (ለምሳሌ ፌስ ቡክና ቱተር) ማሰራጨት ትልቅ ዋጋ ያለ ሥራ ነው። የህወሓት ፀረ-አገር እና ፀረ-ሕዝብ ፕሮጀክቶችን ማሰናከል ሌላ ትልቅ ሥራ ነው። በነፃነት ታጋዮች ላይ የሚደረጉ ዱለታዎችን ማክሸፍ ሕይወት አድን ሥራ ነው። ድርጅቶቹ ውስጥ ሆኖ ድርጅቶቹን ማዳከም የመልካም ዜግነት ግዴታ መወጣት ነው።
በሥርዓቱ ውስጥ ሆነው ኢፍትሃዊነትን ለማጋለጥ እና ሥርዓቱን ለማዳከም ለሚጥሩ ወገኞች አርበኞች ግንቦት 7 ከፍተኛ ክብር አለው፤ ደህንነታቸው እንዲጠበቅም የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል። ፀረ ኢትዮጵያ እና ፀረ ሰው የሆነውን የህወሓትን ሥርዓት ለመጣል እና በምትኩ ፍትህ፣ ነፃነት፣ ዲሞክራሲ፣ እኩልነትና የሀገር አንድነት የተረጋገጠባት ኢትዮጵያን ለማጽናት ከሥርዓቱ ውስጥም ውጭም የሚደረገውን ትግል እናፋፍም።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

mandag 10. august 2015

“በኢህአዴግ ስር ሁኖ እየተሰቃየ የሚገኘው የኢትዮጵያ ህዝብ ወደደም ጠላም ይህ ስርዓት እስከቀጠለ ድረስ መስዋእትነት መክፈሉ አይቀርም ” – ትህዴን

  • 0
     
    Share
arbegnoch ginbot 7
መስዋእትነት አይቀሬ ነው ታሪክ ሰርቶ ማለፍ ግን ክብር ነው!!
የትህዴን ርዕሠ አንቀጽ
በአሁኑ ግዜ በአገራችን ህዝብን የሚወክልና በህዝብ የተመረጠ መንግስት ሳይኖረን ይህንን እድል ለመፍጠር አጋጣሚውን ያገኙ ቡድኖች ሆኑ ግለሰቦች ከህዝብ ፍላጎት እና ከሃገር ጥቅም ይልቅ የግል ጥቅማቸውን‘ና የባእዳኖችን ፍላጎት በማስቀደም ያገኙትን የተለያዩ አጋጣሚዎች በመጠቀም የህዝብን ስልጣን እየነጠቁ ለህዝብ እና ለሃገር የቆሙትን እየገፉ እና እየገደሉ በጉልበት መንግስት ነን በማለት እስካሁን ስልጣን ላይ ይገኛሉ።
የኢህአዴግ አመራሮች ህዝብን የማገልገል ስራ ሳይሆን የየራሳቸውን ጥቅም በማስጠበቅ እና ስልጣን ላይ ወጥተው የህዝብን ሃብት ለግል ጥቅማቸው እያዋሉ፤ ህዝብን እንዳሻቸው እየጨቆኑ፤ እያንገላቱና እየጨፈጨፉ ባጠቃላይ ለትውልድ የሚተርፍ መጥፎ ታሪክና የማይረሳ የጥፋት አሻራ ጥለው እያለፉ መሆናቸው ግልፅ ነው።
የደርግ ስርዓት በህዝብ ልጆች መስዋእትነትና የአካል-መጉደል ከተደመሰሰ በኃላ ስልጣን የሙጥኝ ያለው ፀረ ህዝብ የኢህአዴግ ስርዓት ፋሺስታዊው የደርግ ስርዓት ለሃገር እና ለህዝብ የቆሙትን ንፁኃን ዜጎች በመጨፍጨፍ እንደሚታወቀው ሁሉ አሁን በአገዛዝ ላይ ያለው የኢህአዴግ ስርዓትም በፖለቲካ አመለካከታቸውና ደስ አላሰኙኝም በሚል ንጽሁሃን ዜጎች በድብቅና በግልፅ ብመጥፋት የራሱ የሆነ ጸረ ህዝብ እና ጸረ ሃገር የሆኑ መለያዎች አሉት።
የኢህአዴግ ስርዓት ካለፉት ጨቋኝ ስርዓቶች ለየት የሚያደርጉት በርካታ እኩይ ባህሪያቶች እዳሉት ግልጽ ነው። ስርአቱ የሚታወቅበት መቼም ሊለወጥ እና ሊሻሻል የማይችል አያሌ ጸረ ኢትዮጵያና ጸረ ህዝብ አጀንዳዎች እንዳሉ ሆነው በተጨማሪም አለቆቹ በባእዳን የተነገረውን ትእዛዝ ለማስከበር ሲሉ ለባእዳኖች ባለመገዛቱ የሚታወቀውን የኢትዮጵያ ህዝብ ለመበቀል፤ኢትዮጵያን ለመበታተን’ና ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት የተዘጋጀውን የተሳሳተ ታሪክ ይዞ በተለይም ለስርዓቱ አልገዛም ባለው የኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ቂም ይዞ ለመበቀል ከፍተኛ በጀት እና የሰው ሃይል መድቦ ለጥፋት መነሳቱ የስርዓቱ ባህሪ ነው።
እንደሚታወቀው በመሳሪያ ጋጋታ እና በአፋኝ ህግ ብዛት ሃሳቡን እና ተቃውሞውን እንዳይገልጽ የተከለከለው የኢትዮጵያ ህዝብ ለስርዓቱ ያለውን እምቢተኝነት እና ተቃውሞ ባገኘው አጋጣሚ እየገለጸና ከዛም አልፎ የስርዓቱ አስመሳይ የምርጫ ሂደት ላይ ባለመሳተፍና ባለመምረጥ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ገልጿል። በመሆኑም የኢህአዴ ስርዓት በሚቀጥሉት 5 ዓመታት በስልጣን መቆየቱ የቂሙን ደረጃ የት ያደርሰዋል? ስልጣኑንስ የሚጠቀመው እውነት ሃገር እና ህዝብን ለመጥቀም ነው? ወይስ የተነሳለትን ኢትዮጵያን ህዝቧን የመበታተን ዘመቻውን አጠናክሮ ለማስቀጠል?
ለማኛውም! አጥፊ እና ጠፊ አብረው መኖር እንደማይችሉ ሁሉ መቼም ቢሆን ህዝብ ከኢህአዴግ ስርዓት ጎን ሊቆም አይችልምና ህዝቡ ለኢህአዴግ ባለመምረጡና ከህወሓት-ኢህአዴግ ጎን ባለመቆሙ ምክንያት የተለመደ የኢህአዴግ ቂም በቀል እርምጃ በእጥፍ መቀበሉ አይቀሬ ነው፤ ወያኔ በስልጣን እስካለ ድረስ በህዝቡ ላይ የሚደርሰው የጥፋት ዘመቻ፤ እስራት፤ ድብደባ፤ አፈና፤ በኑሮ ውድነት መሰቃየት፤ ከኖረበት መፈናቀሉ ሌላም ሌላም በከፋ ሁኔታ ይቀጥላል።
በኢህአዴግ ስር ሁኖ እየተሰቃየ የሚገኘው የኢትዮጵያ ህዝብ ወደደም ጠላም ይህ ስርዓት እስከቀጠለ ድረስ መስዋእትነት መክፈሉ አይቀርም ምክንያቱ የእኛ ከኢትዮጵያውያን ታሪክ አንጻር ሲታይ ለውጭ ወራሪውችም ሆነ ለውጥ ጸረ ህዝብ ስርአተወች አሜን ብሎ ተገዝቶ ኣይውቅም ስለዚህ መቼም ቢሆን አይቶ እንዳላየ መሞትን ይመርጣል ተብሎ አይገመትም።
ስለሆነም ማንኛው ኢትዮጵያዊ በሚከተለው ዓላማና በፖለቲካ አስተሳሰቡ ህይወት መክፈሉ ላይቀር እራሱን መስዋእት አድርጎ ብሄራዊ ክብሩን ለማስመለስና በሃገራችን ውስጥ እውነተኛና ያልተገደበ ዴሞክራሲ ለመገንባት፤ ለህዝብና ለሃገር ተቆርቋሪ የሆነ በህዝብ የተመረጠ መንግስት ለመመስረት በሚደረገው ትግል ላይ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆን ይጠበቅበታል፣ ምክንያቱም ለማይቀረው መስዋእትነት ታሪክ ሰርቶ ማለፍ ክብርን ያጎናፅፋልና።
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/45748#sthash.MV5Ni22F.dpuf