søndag 6. desember 2015

ሽግግር ከየት ወዴት? – የኤፍሬም ማዴቦ ንግግር በቪዲዮ

የአርበኞች ግንቦት 7 ከፍተኛ አመራርና በአሁኑ ወቅት አስመራ የሚገኙት አቶ ኤፍሬም ማዴቦ ባለፈው ግንቦት ላይ ስለ ሽግግር መንግስት ንግግር አድርገው ነበር:: ንግግሩ አመት ሊሞላው ቢሆንም በሚዲያ ስላልተለቀቀ ቪዲዮውን ስላገኘነው እንደ አዲስ ለግንዛቤዎ ይረዳ ዘንድ አቅርበነዋል::
a
ሽግግር ከየት ወዴት? – የኤፍሬም ማዴቦ ንግግር በቪዲዮ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/48794#sthash.l94rN5In.dpuf

fredag 4. desember 2015

ጠቅላይ ፍርድ ቤት በአቶ አንዳርጋቸው ላይ የቀረበውን ይግባኝ ውድቅ አደረገ

December 3,2015
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፌደራል አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ምስክር ሆነው እንዳይቀርቡ ያቀረበውን ይግባኝ ዛሬ ህዳር 23/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውድቅ አደርጎታል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በእነ ዘመነ ካሴ መዝገብ ከ2ኛ እስከ 5ኛ ድረስ ለተጠቀሱት ተከሳሾች የመከላከያ ምስክር ሆነው እንዲቀርቡ ተጠይቆ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ በተደጋጋሚ ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡
አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ምስክርነት በተጠሩበት ወቅት የፌደራል አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው በእነ ጀኔራል ተፈራ ማሞ መዝገብ እና በእነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ መዝገብ ላይ ክስ ቀርቦባቸው በእድሜ ልክና በሞት እንዲቀጡ ተወስኖባቸው የህዝባዊ መብታቸው የተሻረ በመሆኑ በምስክርነት ሊቀርቡ እንደማይችሉ መቃወሚያ አቅርቦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ይሁንና ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡላቸው የጠየቁት ለዋስት አሊያም ልዩ አዋቂ ምስክር ሆነው ሳይሆን ነበሩበት የተባለውን ጉዳይ ለመናገር በመሆኑ ለምስክርነት ሊቀርቡ ይገባል በሚል የፌደራል አቃቤ ህግ ያቀረበውን ተቃውሞ ውድቅ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
የልደታ ፍርድ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ሀምሌ 13/2007 ዓ.ም ቀርበው ምስክርነት እንዲሰጡ ከወሰነ በኋላ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ‹‹ትዕዛዝ አልደረሰኝም፣ የተፃፈው ለቃሊቲ ሳይሆን ለአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት የሚል ነው›› እና ሌሎችም ምክንያቶች በማቅረብ በተደጋጋሚ አቶ አንዳርጋቸውን ሳያቀርብ ቀርቷል፡፡ በስተመጨረሻም ጥቅምት 12/2008 ዓ.ም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡ በእነ ዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ እስከ 5ኛ ከተከሰሱት መካከል አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) ውጭ ያሉት የፍትህ ሂደቱ እየተጓተተባባቸው በመሆኑ የአንዳርጋቸው ፅጌ ምስክርነት ቀርቶ በሌሎች መረጃዎች ውሳኔ እንዲሰጥላቸው ሲጠይቁ ሁለቱ ተከሳሾች ግን አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ሊመሰክሩላቸው እንደሚገባ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ አቅርበው ነበር፡፡
በዚህም መሰረት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ለፀረ ሽብር ግብረ ኃይልና አቶ አንዳርጋቸውን ጠይቀውታል ለተባሉት የብሪታኒያ አምባሳደር ደብዳቤ መፃፋቸው ይታወቃል፡፡ ይሁንና ተከሳሾቹ ለሶስቱ አካላት ደብዳቤውን በፃፉበት ማግስት የፌደራል አቃቤ ህግ ከወራት በፊት ለልደታ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ መመስከር አይገባቸውም ብሎ አቅርቦት የነበረውን መከራከሪያ መሰረት በማድረግ አቶ አንዳርጋቸው ምስክር እንዳይሆኑ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠይቆ ነበር፡፡
የአቃቤ ህግን ይግባኝ ያየው ጠቅላይ ፍርድ ቤትም ዛሬ ህዳር 23/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ‹‹አንድ ሰው ለምስክርነት ይቅረብ አይቅረብ በሚል ይግባኝ ሊጠየቅበት አይገባም፡፡ ካስፈለገ ግለሰቡ የሰጡት ምስክረነት መረጃው ተመዝኖ የሚሰጠው ፍርድ ላይ ይግባኝ ሊባል ይችላል፡፡ እኛም ጉዳዩን ለማጣራት ምስክርነቱ እንዲቋረጥ አድርገን የነበር ቢሆንም አሁን ግን እንዲቀጥል ወስነናል፡፡ የአቃቤ ህግን ይግባኝም አልተቀበልነውም›› ሲል ይግባኙን ውድቅ አድርጓል፡፡ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ምስክር መሆን የለባቸውም ብሎ ያቀረበው ክርክር በፍርድ ቤት ውድቅ ሲሆንበት ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡
በእነ ዘመነ ካሴ መዝገብ ከተከሰሱት በተጨማሪ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ ከተከሰሱት መካከል 1ኛ ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ጠርቷቸዋል፡፡ በሌሎች የክስ መዝገቦች ከአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጋር ተገናኝታችኋል የተባሉ ተከሳሾችም አቶ አንዳርጋቸውን የመከላከያ ምስክር አድርገው ሊጠሯቸው እንደሚችሉ የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገልፀዋል፡፡

mandag 30. november 2015

እነ ዘላለም ወርቃገኘሁ መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰሙ! (አንዳርጋቸው ጽጌና እስክንድር ነጋ ለምስክርነት ተጠርተዋል)


esknderበእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት አምስት ተከሳሾች የመከላከያ ምስክሮቻቸውን አቅርበው አሰምተዋል፡፡ በዚህ መዝገብ የተካተቱት ተከሳሾችም ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ዮናታን ወልዴ፣ ባህሩ ደጉ፣ ሰለሞን ግርማ እና ተስፋዬ ተፈሪ ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ ከሰኞ ህዳር 13/2008 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ ለአራት ቀናት ምስክሮቻቸውን ያሰሙ ሲሆን፣ ዘላለም ወርቃገኘሁ 11 ምስክሮች፣ ዮናታን ወልዴ 5፣ ሰለሞን ግርማ 3፣ እና ባህሩ ደጉ እና ተስፋዬ ተፈሪ እያንዳንዳቸው 8 ምስክሮችን ጠርተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም በአንደኛ ተከሳሽ ለምስክርነት የተጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዲቀርቡ አለመደረጋቸው ታውቋል፤ በተጨማሪም በእስር ቃሊቲ የሚገኙትና ለምስክርነት የተጠሩት አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ እና ዳንኤል ሺበሽን ማረሚያ ቤቱ ለተከታታይ ቀናት ከፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ቢተላለፍለትም ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡
በዋናነት ተከሳሾች በማዕከላዊ ፌደራል ወንጀል ምርመራ በነበሩበት ወቅት የደረሰባቸውን አስከፊ የምርመራ ሁኔታና በዚሁ ምክንያት ተገድደው ስለሰጡት ቃል የሚመሰክሩ ምስክሮችን አሰምተዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በዚሁ በምርመራ ወቅት አብረዋቸው ታስረው የነበሩና በኋላ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክር ሆነው ቀርበው የመሰከሩ ግለሰቦች እንዴት ተገድደው በሀሰት እንደመሰከሩባቸው ያስረዱልናል ያሏቸውን ምስክሮች አስደምጠዋል፡፡
ተከሳሾች የተከሳሽነት መከላከያ ቃላቸውን ለፍርድ ቤቱ የሰጡ ሲሆን፣ በተለይ አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ህዳር 16/2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤቱ በሰጠው ቃል፣ የቀረበበት ክስ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው (politically motivated) እንደሆነና በምርመራ ወቅትም በፖሊስና ደህንነት ከተከሰሰበት ጋር በማይገናኝ መልኩ ‹‹ምርጫ 2007ን ለማደናቀፍ ቡድን አደራጅተሃል›› በሚል ሲመረመር እንደነበር አመልክቷል፡፡
ዘላለም በሰጠው ቃል የጸረ-ሽብር ህጉ አሸባሪዎችን ለመከላከልና ለመቅጣት ሳይሆን የተቃውሞ ድምጽ የሚያሰሙ ዜጎችን እና ጋዜጠኞችን ለማጥቃት እየዋለ እንደሆነም አስረድቷል፡፡ ‹‹በእኔ እምነት አሸባሪ ተብሎ የተፈረጀውና ግንኙነት አለህ በሚል የተከሰስኩበት ድርጅት አሸባሪ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ሆኖም ግን እንደ እኔ አይነቶችን ለማጥቃት መጠቀሚያ እንዲሆን ሊፈረጅ ችሏል›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡
ለተከታታይ 41 ቀናት ቀዝቃዛና ጨለማ ክፍል በማዕከላዊ እንዳሳለፈና ለአንድ ወር ከቤተሰብ ጋር እንዳይገናኝ እንደተደረገ የተናገረው ዘላለም፣ ‹‹ለለውጥ የሚታገሉ ወጣቶች ላይ ተጽዕኖ ላለማሳደር የደረሰብኝን በደል ሁሉ እዚህ መዘርዘር አልሻም›› ሲል ገልጹዋል፡፡ በተመሳሳይ ሌሎችም ተከሳሾች በሰጡት ቃል በማዕከላዊ አስከፊ ምርመራ እንደተደረገባቸው አስረድተዋል፡፡
በዚህ መዝገብ የተካተቱት አቶ ባህሩ ደጉ እስካሁን ምስክሮቻቸውን አቅርበው ያላሰሙ ሲሆን፣ አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ እና 6ኛ ተከሳሽ ዮናታን ወልዴ ደግሞ ቀሪ ምስክሮቻቸውን የሚያሰሙ ይሆናል፡፡ ስለሆነም ዛሬ ህዳር 17/2008 ዓ.ም ‹‹ዳኞች አልተሟሉም›› በሚል ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ባለመቻላቸው ለህዳር 24/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
በዚሁ መዝገብ ክስ ተመስርቶባቸው የነበሩት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ እና ዳንኤል ሺበሽ እንዲሁም መምህር አብርሃም ሰለሞን በዚሁ ችሎት ነጻ መሆናቸው ቢበየንም በአቃቤ ህግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ተጠይቆባቸው ጉዳያቸውን በእስር ላይ ሆነው እየተከታተሉ እንዳሉ ይታወቃል፡፡
 
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

søndag 15. november 2015

በረሀብ ለተጠቁ ወገኖቻችን እንድረስላቸው !!!

def-thumb 

በወቅታዊ ሁኔታ ላይ የአርበኞች ግንቦት 7 የአቋም መግለጫ
የኢትዮጵያ ሕዝብ ዳግም ለአስከፊ ረሀብና ችጋር ተጋልጧል፤ ስፋት ጥልቀቱ በ70ዎቹና 80ዎቹ ከነበሩት ጋር ይስተካከላል ተብሎ ተፈርቷል። ከአሁኑ ሰው በረሀብ መሞት መጀመሩ ከአራትና አምስት ወራት በኋላ የሚመጣውን አደጋ ከባድነት መገመት ያስችላል።
ለአስር ተከታታይ ዓመታት ከአስር በመቶ በላይ ዓመታዊ የኢኮኖሚ እድገት በማምጣት ዓለምን እየመራን ነው የሚለው ዓይን ያወጣ ውሸት፤ “ድህነትን ተረት እናደርጋለን” የሚለው ጉረኛ መፈክር፤ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ራድዮ “የህዳሴ ብስራቶች”፣ የአባይ ግድብና የከተማ ባቡር ግንባታ ዜናዎች ለኢትዮጵያዊው አርሶ አደር ቁርስ፣ ምሳና እራት አልሆኑም።
“አድገናል”፣ “ተመንድገናል”፣ “በምግብ ራሳችንን ችለናል” ሲል የከረመው የህወሓት አገዛዝ የረሀቡ ዜና አፈትልኮ ሲወጣ እና የዓለም መገናኛ ብዙሀን መነጋገሪያ ሲሆን የተራበውን ወገናችንን ለማብላት ከመሯሯጥ ይልቅ ተፈጥሮ ላይ ማላከኩን ተያይዞታል። ከዚህ አልፎ ዓመታዊ ድግሶቹ እና ለባለሥልጣናቱ የሚሰጡ ጥቅማጥቅሞች ጉዳይ ከረሀብ በላይ አሳሳቢ በመሆኑ 15 ሚሊዮን የሚገመት ሕዝብ በሞት አፋፍ ላይ እያለ የአገሪቱ ሀብት ለድግስና ፈንጠዚያ እንዲሁም ለእያንዳንዱ ባለሥልጣን ቤተመንግሥት አከል መኖሪያ ቤት ማሠሪያ እየዋለ ነው። መቀሌ ላይ ህወሃት 40ኛ ልደቱን ለማክበር ወደ ግማሽ ቢልዮን ብር ባወጣ ማግስት በአማራ ስም ለወያኔ ባርነት የገባው ብአዴን 300 ሚሊዮን ወጪ በማድረግ በረሃብተኛው ሕዝብ አናት ላይ እየጨፈረ ነው:: ይህ የኢትዮጵያን ሕዝብ መናቅ ብቻ ሳይሆን ደግሞ ደጋግሞ ከመግደል የሚቆጠር ወንጀል ነው።
ለመሆኑ የአየር ንብረት መዛባት እየተደጋገመ ለሚመጣ ችጋርና ቸነፈር በቂ ምክንያት ሆኖ ያውቃልን? ለምንድነው ፍትህና ነፃነት በሰፈነባቸው አገሮች ውስጥ ዝናብ ጠፍቶ የእርሻ ምርት ቢቀንስ እንኳን ሰው በረሀብ የማይሞተው? አስከፊ የረሀብ ዜናዎች የሚሰማባቸው አገሮች በሙሉ ነፃነት የታፈነባቸው አገሮች መሆናቸውስ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው? ለምንድነው ተደጋግሞ ከሚመጣ የረሀብ አዙሪት መውጣት ያቃተን?
የእነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መልስ አጭርና ቀጥተኛ ነው። ለችግሮች መፍትሄ መሻት የሚቻለው በነፃነት ማሰብ የሚችል ጭንቅላት ሲኖር ነው። በባርነት ጨለማ ውስጥ ያለ ጭንቅላት ለችግሮች መፍትሄ የማፍለቅ አቅም የለውም። እንዲያውም እንዲህ ዓይነቱ ድኩም ጭንቅላት ችግሮችን ማሸነፍ ሳይሆን ተሸናፊነትን ተቀብሎ ከችግሮች ጋር ተስማምቶና ተወዳጅቶ መኖርን ይመርጣል። ለዚህም ነው የአስተዳደር በደልና ረሀብ ምክንያትና ውጤት ብቻ ሳይሆን እጅና ጓንትም ጭምር የሆኑት።
ነፃነት ያለው ሕዝብ ረሀብን እንደሚያሸነፍ ተደጋግሞ የታየ ጉዳይ ነው። ለዚህም ነው ረሀብን የተፈጥሮ ሚዛን መዛባት ውጤት ብቻ አድርጎ ማቅረብ እውነትን መሸፈጥ የሚሆነው። ረሀብ የብልሹ አስተዳደር ውጤት መሆኑ ያፈጠጠ፣ ያገጠጠ ሀቅ ነው። ከረሀብ መገላገያ መንገድም የተበላሸ አስተዳደር ተወግዶ ኃላፊነት የሚሰማው፣ የዜጎች የማሰብ ነፃነት የሚያረጋግጥ ሕዝባዊ አስተዳደር ሲኖር ነው።
አገራችን ኢትዮጵያን የረሀብ ቀጠና ካደረጉ የ24 ዓመታት የወያኔ “የዘርፈህ ብላ” የኢኮኖሚ ፓሊሲ ውጤቶች መካከል አንዳንዱን ለአብነት ያህል መዘርዘር ይቻላል።
1.ገበሬና መሬት ተለያይተዋል። ኢትዮጵያዊያን አርሶ አደሮች መሬት አልባ ሆነዋል። ለም መሬቶች በኢንቨስትመንት ስም ለህወሓት ጉልተኞችና ምስለኔዎቻቸው ታድሏል፤ እነሱ ደግሞ በተራቸው ለባዕዳን ሽጠውታል። ኢትዮጵያዊው አርሶ አደር በሀገሩ ጭሰኝነት እንኳን አጥቶ ለቀን ሠራተኝነትና ልመና ተዳርጓል። በዚህም ምክንያት ገበሬው እንኳንስ ትልቁን የአየር መዛባት ትንሿንም የዋጋ ንረት መቋቋም እስከማይችልበት ደረጃ ተዳክሟል።
2.ዘርን መሠረተ ባደረገ ክልላዊ ድንበር ሳቢያ ኢትዮጵያዊው ጎበዝ አርሶ አደር አንዱ ቦታ ቢከፋ ወደ ተሻለ ቦታ ተዛውሮ ማረስ አልቻለም። ከሰሜን ወደ ደቡብ ከሄደ የአገራችን አርሶ አደር ይልቅ ባህር ተሻግሮ የመጣ ኤንቨርስተር ነኝ ባይ መሬት ማግኘት ይቀለዋል። እንዲያውም ኢትዮጵያዊው ገበሬ በዱላና በጥይት ሲባረር፤ ከባዕድ አገር የመጣው ብድርና ማበረታቻዎች ይሰጠዋል።
3.የህወሓት ባላሥልጣኖችና በየቦታው ያስቀመጧቸው ምስለኔዎቻቸው ራሳቸውን ባለሚሊዮኖች፣ ከፍ ሲልም ባለ ቢሊዮኖች አድርገዋል። እነዚህ በአንድ ጀምበር ከትቢያ የተነሱ ቱጃሮች ከገንዘብ በተጨማሪም የጄኔራልነት፣ የሚኒስቴርነት፣ የክልል ገዢነት፣ እጅግ ቢያንስ የቢሮ ኃላፊነት ሥልጣንን ኪሳቸው ውሰጥ ከተዋል። የመንግሥት ሥልጣንና ሃብት ይኸን ያህል የተቆራኙበት ሥርዓት በኢትዮጵያ ኖሮ አያውቅም። የጥቂቶች ያለአገባብና ያለቅጥ መክበር በአንፃሩ ደግሞ የብሃኑን ሕዝብ መደህየት ረሀብ እጣ ፈንታችን እንዲሆን አድርጓል።
4.በአቋራጭና በፍጥነት ለመክበር አስተማማኙ መንገድ የገዛ ራስ ጥረትና ታታሪነት ሳይሆን ቅጥፈት፣ አጭበርባሪነትና ሎሌነት ማደር መሆኑን የህወሓት አበጋዞች በተግባር እያሳዩ ሠርቶ፣ ለፍቶ ማደግ ሞኝነት እንዲሆን አድርገውታል። በዚህም ምክንያት በባህላችን ውስጥ ኮትኩተው ያሳደጓቸው አድርባይነት፣ ስንፍናና እና ልመና ችግርን የመጋፈጥ አቅማችንን ሰልበውታል።
5.ደኖቻችን ተጨፍጭፈው፣ ለም መሬታችን ተሸርሽሮ በማለቁ የግብርናችን ምርታማነት በእጅጉ ቀንሷል። በህወሓት የአገዛዝ ዘመን የደን ጭፍጨፋና የመሬት መሸርሸር በአስደንጋጭ ሁኔታ ጨምሯል። አገሪቷ በፍጥነት ወደ ምድረበዳነት እየተቀየረች ነው።
6.ኢትዮጵያዊያን ገበሬዎች ድርቅን መቋቋም ስለሚችሉ ሰብሎች ወይም የአስተራረስ ዘዴዎች ማሰብ፣ መመራመርና መፈተሽ አይችሉም። አዲስ ነገር መሞከር “የኢህአዴግ የግብርና ፓሊሲን“ በመቃወም ወንጀል የሚያስቀጣ ተግባር ሆኗል። በዚህም ምክንያት ገበሬው ድርቅን መቋቋሚያ አዳዲስ ዘዴዎች መፈለግ ቀርቶ በተለምዶ የሚያውቃቸውንም መጠቀም አልቻለም።
7.የህወሓት አገዛዝ፣ እንደ ኢኮኖሚው ሁሉ የኢትዮጵያን ሕዝብ ብዛት ሊቆጣጠር የሚሞክረው ቢሮ ውስጥ ቁጭ ተብሎ በሚደረግ የቁጥር ጨዋታ ነው። አገዛዙ ውጤታማ የስነ ሕዝብ ፓሊሲ የለውም፤ እንኳንስ የቀጣይ ዓመታት የሕዝብ እድገት ምጣኔን ሊቆጣጠር አሁን ያለነው ቁጥራችን ስንት እንደሆነ እንኳን በትክክል ሊነግረን አልቻለም፤ ረሀብ ነው መብዛታችንን እየነገረን ያለው።
አርበኞች ግንቦት 7፡ የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ እነዚህና የመሳሰሉት ጭብጦችን በማንሳት የረሀቡ መሠረታዊ ምክንያት የህወሓት አገዛዝ ያሰፈነው ብልሹ አስተዳደር መሆኑን በአንጽዖት ይናገራል። ሕዝባችን በነፃነት ማሰብ፣ መመራመር፣ መፈተሽ ቢችል ኖሮ ረሀብን መከላከያ ብልሃት ማግኘት ባላቃተውም ነበር ብሎ አርበኞች ግንቦት 7 ያምናል። ረሀብን ለማጥፋት ህወሓትን ከሥልጣን ማስወገድ ከምንጊዜውም በላይ ወሳኝ የሆነ ጊዜ ላይ ተደርሶአል ብሎ አርበኖች ግንቦት 7 ያምናል።
ነገር ግን ረሀብ ጊዜ አይሰጥም። የፓለቲካ ሥርዓት ለውጥ በሞት አፋፍ ላይ ላለ ወገናችን መፍትሄ አይሆንም። ስለሆነም ለረሀቡ መሠረታዊ መፍትሄ የሆነውን ትግላችንን ሳንዘነጋ የወገኖቻችንን ሕይወት ለመታገድ የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ ያደርጋል። ሲቪክ ማኅበራት የተራበው ወገናችን የወያኔ መጠቀሚያ ሳይሆን የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ የሚያገኝበት መንገድ እንዲያፈላልጉ እና ወገን ለወገን የሚቆምበትን ዘመቻ እንዲያስተባብሩ ጥሪ ያደርጋል። ለወገኖቻችን የሚላከው እርዳታ ከዚህ በፊት እንደነበረው ሁሉ ወደአገዛዙ ባለሥልጣኖች የግል ኪስ እንዳይፈስ ጥንቃቄ እንዲደረግ ያሳስባል። ለወገኖቻችን ለመድረስ እያንዳንዳችን በግል፤ እንዲሁም በቡድን የተቻለንን ሁሉ እናድርግ።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
ኅዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም.

søndag 25. oktober 2015

የኢሳት 5ተኛ አመት በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ በተሳካ ሁኔታ ተካሄደ!


 ዲቦራ ለማ/ኖርዌ

አርቲስና አክቲቪስት ታማኝ በየነ እንዲሁም ታዋቂው የኢሳት ጋዜጠኛ አፈወርቅ አግደው በተገኙበት ኢሳት የተቋቋመበትን የአምስተኛ አመት በአል በደማቅ ሁኔታ በኦክቶበር 24፣ 2015 በኦስሎ ከተማ ተካሄደ። በዝግጅቱ ላይ ከተለያየ የኖርዌ ከተማዎች የመጡ በርካታ ታዳሚዎች ተገኝተውበታል።



ዝግጅቱ በኖርዌ የሚኖሩ ታዳጊዎች ኢሳት የተመለከተ ዝማሬ አቅርበው ታዳሚውን ያስደመሙ ሲሆን በመቀጠል በኖርዌ የኢሳት ኮሚቴ ሊቀመንበር የእንኳን ደህና መጣችሁና የመግቢያ ንግግር በማድረግ ፕሮግራሙን ጀምሯል። በመቀጠል የተለያዩ አዝናኝና አስተማሪ መጣጥፎችና ግጥሞች እንዲሁም አጭር ጭውት በዝግጅቱ ላይ ቀርቧል። ለገቢ ማሰባሰቢያው የሚውል የምግብና መጠጥ ሽያጭ፣ የተለያዩ ቁሳቁሶች ሽያጭ እንዲሁም የትኬት ሽያጮች ተካሂዷል።

ጋዜጠኛ አፈወርቅ አግደው የሚያስደንቅ ስራውን በመድረክ ያቀረበ ሲሆን አርቲስት ታማኝ በየነም የተለያዩ መረጃዎችን ለህዝቡ አቅርቧል። የጨረታው ሰአት ሲደርስ ጨረታውን አርቲስት ታማኝ በየነ የመራ ሲሆን በጨረታው ላይ በርካታ ተሳታፊዎች ተሳትፈዋል። የጨረታውን ዋንጫ ያቀረቡት በኖርዌ በርገን ከተማ ነዋሪ የሆኑ የኢሳት ቤተሰቦች ሲሆኑ በመድረክላይም ኢሳት ይቀጥላል የሚል የራሳቸውን ዝማሬ አቅርበዋል።

ከጨረታ፣ ከምግብና መጠጥ ሽያጭ፣ እንዲሁም ከትኬት ሽያጭ እንዲሁም ከተለያዩ ነገሮች ሽያጭ ለኢሳት ከፍተኛ ገቢ ተገኝቷል። ዝግጅቱ በደማቅ ሁኔታ በኖርዌይ የሰአት አቆጣጠር ከምሽቱ 23፡00 ተጠናቋል።



ኢሳት በእኛ ድጋፍ ይቀጥላል!!

tirsdag 20. oktober 2015

አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ለሁለተኛ ጊዜ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት አስመረቀ

October 20, 2015
የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ
Professor Berhanu Nega with Patriotic Ginbot7 fighters
አርበኞች ግንቦት 7 በሁለት ድርጅቶች ማለትም በኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር እና በግንቦት 7 ንቅናቄ ውህደት ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም ከተመሰረተ በኋላ ከትናትና በፊት እሁድ ዕለት ጥቅምት 7 ቀን 2008 ዓም ለሁለተኛ ጊዜ ብዛት ያላቸውን አርበኛ ታጋዮች ለሦስት ወራት አሰልጥኖ አስመርቋል፡፡
እነዚህ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሁለተኛ ዙር ተመራቂ አርበኛ ታጋዮች ለሦስት ተከታታይ ወራት የተሰጣቸውን የፖለቲካ፣ የወታደራዊ እና ሌሎች ተያያዥ የሆኑ የመረጃና ደህንነት ትምህርቶችን በሚገባ ወስደው በሁሉም መስክ አመርቂ ውጤት በማስመዝገብ ነው ሊመረቁ የቻሉት፡፡
እጅግ በጣም ደማቅ በሆነ ስነ-ስርዓት በተከናወነው የምረቃ በዓል ላይ ከተለያዩ ቦታዎች ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች የታደሙ ሲሆን የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ሊቀመንበር አርበኛ ታጋይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና የድርጅቱ የትምህርትና ስልጠና መምሪያ ኃላፊ አርበኛ ታጋይ ተስፋሁን ተገኝ ንግግር በማሰማት ለተመራቂ አርበኛ ታጋዮች መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ከውህደቱ ኋላ የመጀመሪያውን ዙር ሰልጣኞች ያስመረቀው ግንቦት 2 ቀን 2007 ዓ.ም መሆኑ ይታወቃል፡፡
Patriotic Ginbot7 fighters

onsdag 14. oktober 2015

በእነ ሀብታሙ አያሌው ላይ ተረኛ ችሎት የወሰነውን ይግባኝ ሰሚ ሻረው

የአቃቤ ህግ ይግባኝ ያስቀርባል ወይስ አያስቀርብም የሚለው ጥቅምት 17/2008 ይወሰናል
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ እንዲሰናበቱ የተበየነላቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ላይ አቃቤ ህግ ይግባኝ ጠይቆ በተረኛ ችሎት ይግባኙ ያስቀርባል ቢባልም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ይህንን ውሳኔ በመሻር ያስቀርባል ወይስ አያስቀርብም የሚለውን ለመበየን ለጥቅምት 17/2008 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
Habtamu abrhayeshiwas daniel
ዛሬ ጥቅምት 3/2008 ዓ.ም የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የቀረቡት የፓርቲ አመራሮቹ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና አብሯቸው ይግባኝ የተጠየቀበት አብርሃም ሰለሞን ዛሬ የቃል ክርክር እንደሚያደርጉ የሚጠበቅ የነበር ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ ግን በነሀሴ 15/2007 ዓ.ም ተረኛ ችሎት ይግባኙ ያስቀርባል ያለውን ውሳኔ ወደ ጎን በመተው አቃቤ ህግ የይግባኝ አቤቱታውን እንደገና እንዲያሰማ አድርጓል፡፡
በመሆኑም አቃቤ ህግ የስር ፍርድ ቤት በአቃቤ ህግ የቀረቡትን የቴክኒክና የሰነድ ማስረጃዎች ይዘት በአግባቡ ሳይመረምር ውሳኔ ስለሰጠብን ውሳኔው አግባብ ስላልሆነ ይግባኝ ሰሚ ችሎቱ እንዲመረምርለት ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ይህንኑ የይግባኝ አቤቱታ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 17/2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል በነጻ እንዲሰናበቱ የተበየነላቸው ተከሳሾች እስካሁን በእስር ላይ የቆዩበት ምክንያት አግባብ ስላልሆነ አቤቱታ እንደሚያቀርቡ ተከሳሾች ገልጸዋል፡፡ እስካሁን በእስር ላይ ሊቆዩ የቻሉት ተረኛ ችሎቱ በሰጠው እግድ መሆኑ ቢገለጽም፣ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ግን አቤቱታው እንዲቀርብ ፈቅዷል፡፡ ተረኛ ችሎቱ ነሀሴ 15/2007 ዓ.ም ብይኑን ሲሰጥ ተከሳሾች ችሎት ሳይቀርቡ እንደነበር ይታወሳል፡፡
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47406#sthash.fJjDuUvj.dpuf

tirsdag 13. oktober 2015

ሐብታሙ አያሌው በኩላሊት ጠጠር መታመሙ ተገለጸ * እነ አብርሃ ደስታ ነገ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ

  • 27
     
    Share
habtamu ayalew
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47386#sthash.GZ4e0GZW.dpuf
(ዘ-ሐበሻ) በ እስር ቤት የሚገኘው ታዋቂው ፖለቲከኛ ሃብታሙ አያሌው ዛሬ በድንገተኛ ህመም ዘውዲቱ ሆስፒታል ተወስዶ እንደነበር ተዘገበ:: በአዲስ አበባ የሚገኙ የዘ-ሐበሻ ምንጮች እንዳሉት ሃብታሙ ከ እስር ቤት ወደ ዘወዲቱ ሆስፒታል የተወሰደበት ምክንያት በሁለቱም ጎኖቹ ላይ የህመም ስሜት ስለተሰማው ነበር:: የዘውዲቱ ሆስፒታል የህክምና ባለሙያዎች ምርመራ ካደረጉለት በኋላ ህመሙ የኩላሊት ጠጠር መሆኑን ለባለቤቱ ወ/ሮ ቤተልሄም መናገራቸውን እነዚሁ ምንጮች አብራርተዋል:: ሃብታሙ ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የተመለሰ ሲሆን በነገው ዕለትም ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ተገልጿል:: ከሃብታሙ አያሌው ጋር አብረው የተከሰሱትና በቅርቡ በከፍተኛው ፍርድ ቤት በነፃ የተለቀቁት አብርሃ ደስታ; ዳንኤል ሺበሺና የሺዋስ አሰፋም በነገው ዕለት አቃቤ ሕግ ይግባኝ በጠየቀባቸው ክስ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀርበው የቃል ክርክር ያደርጋሉ ሲሉ የዘ-ሐበሻ ምንጮች አስታውቀዋል:: 


søndag 4. oktober 2015

ኢሳት በእኛ ድጋፍ ይቀጥላል!!


ኦክቶበር 2, 2015
ዲቦራ ለማ/ኖርዌ/

አለማችን አሁን ያለችበት ዘመን በከፍተኛ  ደረጃ መረጃ ከአንዱ ወደ አንዱ በየሰከንዱ እየፈሰሰ አለምን ወደ አንድ ጎራ አምጥቶ የመረጃን ጠቃሚነት እያየን የመጣንበት ጊዜ ነው። መረጃ የአንድን ሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፓለቲካዊ እንቅስቃሴን ለማዳበር ከፍተኛውን ሚና ይጫወታል።

እንደሀገራችን ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት ደግሞ በተቃራኒው መረጃ ለህዝብ እንዳይደርስ የመረጃ መረቦችን በሙሉ በመበጣጠስና በማገድ ትክክለኛ መረጃ ለህዝብ እንዳይደርስ ሲከላከሉ እናያለን። በሀገራችን ኢትዮጵያ ያለው የመረጃ ምንጭ አንድ የገዥው ፓርቲ ልሳን የሆነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዝንና ራዲዮ ሲሆን ሌሎችም የስርአቱ አቀንቃኝ የሆኑ እንደ ሬዲዮ ፋና ያሉ የግል ልሳናት አሉ። እነኚህ የወያኔ ልሳኖች አርባ ስምን ሰአት ያለምንም እፍረት የስርአቱን ፕሮፓጋንዳ ሲያሰራጩ ውለው ያድራሉ።
ህዝቡ ትክክለኛ መረጃ እንዳያገኝ ከፍተኛ ጫና በማሳደርና የህዝቡን ንብረት በመዝረፍና ህዝቡን ጦም በማሳደር በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር በመክፈል ትክክለኛ መረጃ እያቀረበልን የሚገኘውን የኢሳትን ጣቢያ በተደጋጋሚ በማፈን ስርጭቱን ለማቋረጥ ወያኔ ብዙ ሙከራ ሲያደርግ መቆየቱ ይታወቃል።

ሆኖም ግን ኢሳት በህዝብ ድጋፍ ዛሬም ትክክለኛ መረጃን እያደረሰ የህዝብ አይንና ጆሮ ሆኖ ቀጥሏል። አምባገነኑ የወያኔ ስርአት ትክክለኛ መረጃን ለህዝብ የሚያቀርቡ ጋዜጠኞችንና ፀሀፊዎችን በእስር በማንገላታትና ከሀገር በማሰደድ መረጃን ሊያጠፋ ቢሞክርም ኢሳት ግን ዛሬም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ጨምሮ በሀገሪቱ ላይ የሚሰሩ ወንጀሎችን በማጋለጥ ለህዝቡ መረጃን እያቀረበ ይገኛል።

ኢሳት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ተደማጭነት ያለውና አንድ ብቸኛ ትክክለኛ መረጃ አቅራቢ ተቋም ሆኖ በህዝብ ድጋፍ የሚንቀሳቀስ የህዝብ ሀብት ነው። ኢሳት በዚህ መልኩ በብዙ መሰናክሎች ውስጥ አልፎ  እነሆ ዛሬ 5ተኛ አመቱን በተለያዩ ሀገራት እያከበረ ይገኛል። በኦክቶበር  24, 2015 ደግሞ የኖርዌ ዋና ከተማ በሆነችው ኦስሎ ኢሳት 5ተኛ አመቱን በከፍተኛ ሁኔታ ለማክበር በዝግጅት ላይ ይገኛል። በመሆኑም በኖርዌ በተለያዩ ከተሞች የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ወደዚህ ዝግጅት ተጋብዛችኋል።

የአምባገነኖችን እድሜ ለማሳጠርና ዲሞክራሲያዊ መንግስት ለመመስረት ትክክለኛ መረጃ ለሀገራችን ህዝብ ወሳኝ በመሆኑ ኢሳት እንዲቀጥል የሁላችንም ተሳትፎ አስፈላጊ በመሆኑ በስፍራው ተገኝተን የበኩላችንን አስተዋፅኦ እናድርግ ብዬ ጥሪዬን አቀርባለሁ።



መረጃ ኃይል ነው


በእኛ ድጋፍ ኢሳት ይቀጥላል!!!!

ድርጅታችንን እናጠንክር፤ በጽናት እንታገል!

ድርጅታችንን እናጠንክር፤ በጽናት እንታገል!
October 4, 2015
def-thumb“የአርበኞች ግንቦት 7 አባል በመሆኔ እኮራለሁ” እያሉ በአገዛዙ የይስሙላ ችሎት ሳይቀር በድፍረት የሚናገሩ ወጣቶች ተፈጥረዋል። ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለዲሞክራሲ፣ ለእኩልነትና ለሀገር አንድነት መስዋዕትነት መክፈል የሚያኮራ ተግባር መሆኑ በተግባር የሚያሳዩ ወጣቶች መጥተዋል፤ አሁን በርካቶችም እየመጡ ነው። ወያኔ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በማኅበረሰባችን ውስጥ የዘራው የፍርሀትና የአድርባይነት ስሜት በራሱ በወያኔ የአገዛዝ ዘመን ተወልደው ባደጉ ወጣቶች እየተናደ፤ በምትኩ ሊጠፋ ተቃርቦ የነበረው የአገር ፍቅርና የአርበኝነት ስሜት እያንሰራራ ነው።
ቅንነት፣ ሀቀኝነት እና ጽናት ከተጣሉበት ጉድጓድ አቧራቸውን አራግፈው እየተነሱ ነው። በማኅበረሰባች ውስጥ ትልቅ የስነልቦና አብዮት እየተካሄደ ነው።
ከስነልቦና ለውጡ ጋርም በተግባር የአገር አድን ሠራዊትን የመቀላቀል ፍላጎት ያላቸው ወጣቶች ቁጥር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ ነው። ወጣቶች የአገራቸው ባለቤት መሆናቸው ተገንዝበው የፓለቲካ ሥርዓት ለውጥ ለማምጣት በቁርጠኝነት መነሳታቸው ተስፋ ሰጪ ነገር ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 በዚህ የለውጥ ወቅት ውስጥ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ አጽንዖት ልንሰጣቸው ስለሚገቡ የድርጅትና የሥነሥርዓት (ዲሲፕሊን) አስፈላጊነት ላይ የጋራ ግንዛቤ መያዝና በተግባርም መተርጎም አስፈላጊ ነው ብሎ ያምናል።
ወጣቶች ትግሉን ለመቀላቀል መሻታቸው መልካም ነገር ነው። ሆኖም ግን በድንገት ብድግ ብለው መንገድ ከመጀመር ይልቅ ከሚያምኗቸው ወዳጆቻቸው ጋር የመሠረቱት፤ ከአርበኞች ግንቦት 7 ጋርም ትስስር የፈጠረ ስብስብ አካል ሆነው መቆየታቸው እጅግ አስፈላጊ ነው።
በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ ሆኖ የሚስጢር ድርጅት ማዋቀር አስቸጋሪ መሆኑ የማያጠራጥር ቢሆንም የማይቻል ነገር ግን አይደለም። ወጣቶቻችን በአምባገነን ሥርዓት ውስጥም ሆነው በዲሲፕሊን የታነፀ ድርጅት የመፍጠርን ክህሎት መላበስ ይገባቸዋል። ይህንን ማድረግ ስንችል ነው የህወሓትን ፀረ-አገርና ፀረ-ትውልድ ተግባር ማክሸፍ የምንችለው። ትግሉን በሁሉም የኢትዮጵያ ግዛቶች ማቀጣጠል የምንችለው በየአካባቢው የተደራጀ የለውጥ ኃይል ሲኖረን ነው። ስለሆነም የምስጢር የተደራጀ አካል በየመኖሪያና የሥራ አካባቢዎቻችን ሁሉ እንዲኖር ማድረግ ከአጣዳፊ ሥራዎቻችን አንዱ እናድርገው።
ሁለተኛው ነጥብ ሥነሥርዓትን የሚመለከት ነው። ሥነሥርዓት ከሌለ ድርጅት የለም። የህወሓት አገዛዝ ያሳደረብን ጎጂ የባህል ተጽዕኖ ከባድ በመሆኑ ራሳችንን በሥነሥርዓት ለማነጽ መልፋት ይጠበቅብናል። አገራችንና ራሳችንን ከህወሓት አገዛዝ ነፃ አውጥተን የተሻለ ሥርዓት ማምጣት የምንችለው ራሳችን፣ ድርጅታችን እና ተግባሮቻችን ለሥነሥርዓት ተገዢ ስናደርግ ነው። የነፃነት ታጋዮች ራሳቸውን ለሥነ ሥርዓት ያስገዙ መሆን ይኖርባቸዋል። አስተሳሰባችን ራሱ ሥነ ሥርዓት የያዘ ሊሆን ይገባዋል። እንደዚሁም ሁሉ ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት የታነጹ ሊሆኑ ይገባል።
የንቅናቄዓችንን መዋቅር በመላው አገራችን ከዘረጋን፤ ራሳችንን፣ አስተሳሰቦቻችንና ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት ከመራን፤ ቅንነት፣ ሀቀኝነትና ጽናት ከተላበስን ድላችን ቅርብ እና አስተማማኝ ነው። ለውጥን የሚናፍቅ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራት ይተግብር።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

torsdag 24. september 2015

በወያኔ ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ የሰራዊት አመራሮችና በመከላከያ ሰራዊቱ መካከል አለመተማመን እና ጥርጣሬ ተስፋፍቶል

September 24,2014
በወያኔ ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ የሰራዊት አመራሮችና በመከላከያ ሰራዊቱ መካከል አለመተማመን እና ጥርጣሬ መስፋፋቱን ውስጥ አዋቂ ምንጮች አስረድተዋል:: የሕዝብን መብት እና በልማት ስም በፕሮፓጋንዳ በመደለል በስልጣን ላይ ያለው በወያኔው አመራሮችና እና በመከላከያ ሰራዊቱ መካከል አለመተማመን እና ጥርጣሬው እየሰፋ መምጣቱን ለምድር ጦር ክፍል ቅርብ የሆኑ ምንጮች ገልፀው። ባለፉት አመታት በሰራዊት ውስጥ ወታደራዊ ደህንነቶች መሰግሰጋቸው ከሰራዊቱ ጥያቄዎች ጋር ተደምሮ በተለይ በምስራቅ ደቡብ እዝ እና በሰሜን እዝ ከፍተኛ የሆነ የውስጥ ውጥረት እንዳለና እንዲሁም በሰራዊቱ ውስጥ በየስብሰባው ሶማሊያ ስለዘመቱ ወታደሮች ማብራሪያ መጠየቁን ታውቋል::
በሰራዊት ውስጥ በወታደራዊ ደህንነት ቦታ የሚያገለግሉ ምንጮች እንዳሉት ሰራዊቱ ውስጥ የተከሰተው አለመተማመን እና ጥርጣሬ እየጨመረ የመጣው አሁንም በየእዙ የሚጠረጠሩ መኮንኖች እስራት እንደቀጠለ ተናግረዋል::ለሆዳቸው ያደሩ የሰራዊት አባላት ቢኖሩም ይህን ያህል አይደሉም የሚሉት ምንጮቹ ሰራዊቱ ግን በመፈራራት እና እርስ በርስ ጥርጣሬ ውስጥ እየተጓዘ እንደሆነ ገልጸዋል::በተለያዩ ግምገማዎች ከ10 የሰራዊቱ አባላት ሰባቱ በማስጠንቀቂያ መታለፋቸውን በራሱ በሰራዊት ውስጥ ያለው ችግር አንደኛው ገጽታ መሆኑም አውስተዋል::

fredag 18. september 2015

ህወሃት ጦርነት ጀመረ፣ ቁስለኞች ታይተዋል


“ሕዝብ አስፈቅደን ውጊያ እንጀምራለን” ሃይለማርያም
omhajer


በነጻ አውጪ ስም አገር እየገዛ ያለውን የትግራይ ነጻ አውጪ ግምባር (ህወሃትን) ለመውጋት ብረት ያነሳው ሌላ የትግራይ ነጻ አውጪ ሃይል /ትህዴን ወይም በትግሪኛ ዴምህት/ መሪ የነበረው “ተጋዳላይ” ሞላ አስገዶም ህወሃትን ከተቀላቀለ ጥቂት ቀናት በኋላ ጦርነት መጀመሩ ተሰማ። የህወሃት ወኪል ሃይለማርያም ደሳለኝ ውጊያው የሚጀመረው የህዝብ ፈቃድ ተጠይቆ እንደሚሆን ተናግረው ነበር።
የጎልጉል መረጃ አቀባዮች ከአዲስ አበባ እንደገለጹት ጦር ኃይሎች ሆስፒታል ቁስለኞች እየገቡ መሆኑንን እማኞች ነግረዋቸዋል። ጦርነቱ በየትኛው መንደርና ወረዳ እንደተጀመረ ለይተው ያላስረዱት የዜናው ባለቤቶች፣ ውጊያ እየተካሄደ ያለው ኤርትራ ምድር ላይ እንደሆነ ግንአልሸሸጉም።
አንድ የሆስፒታል ሰራተኛ ዘመድ ደውሎላቸው “ቁሰለኞች አሉ ሥራ በዝቶብኛል” ማለታቸውን የጎልጉል መረጃ ሰጪዎች ከአዲሰ አበባ ገልጸዋል። ባለፈው ሳምንት በሁመራ አቅጣጫ የከባድ መሳሪያ ተኩስና ድብደባ መሰማቱን የተለያዩ ድረገጾች ዘግበው ነበር። ይህ ሁሉ ከመሆኑ በፊት ሻእቢያ “ህወሃት ሊወረኝ ነው” ሲል ክስ ማሰማቱ አይዘነጋም።
ኦምሃጀር በሚባለው ስፍራ የከረረ ውጊያ እየተካሄደ መሆኑን እንደሰሙ የገለጹ በውጊያው የትኛው ወገን ድል እንደተቀዳጀ ለጊዜው መናገር እንደማይቻል አመልክተዋል። ውጊያው ጠርዙን አስፍቶ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።
four front mapከህወሃት በኩል ውጊያው ከሻዕቢያ ጋር እንደሆነ ቢገለጽም ከሌላ ወገን “ህወሃትን የወጋሁት እኔ ነኝ” ባይ ይህ ዜና እስከታተመ ድረስ አልተሰማም። የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ህወሃትን በነፍጥ አንበረክካለሁ በማለት ማወጁና አመራሮቹም ወደ ውጊያው አውድ ማምራታቸው ይታወቃል። ህወሃት ኤርትራን በአራት አቅጣጫ የመውጋት እቅድ እንዳለው ጎልጉል መዘገቡ የሚታወስ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በርካታ የሰራዊቱ አባላት ከሰራዊቱ እየሸሹና እየተሰወሩ መሆናቸው ህወሃትን እንዳሳሰበው፣ ጦሩ የመዋጋት ፍላጎት ያጣል የሚል ሥጋት እንዳለ የሚጠቁሙ ክፍሎች “የአሁኑ የውጊያ አቅጣጫ በዚህ መልኩ እንዲሆን መደረጉ ይህንኑ ለመፈተንም ጭምር ነው” ብለዋል።
በሌላ ዜና በሶማሌ ያለው ሰራዊት የመመለስ ጥያቄ ማንሳቱና ሁለት ጄኔራሎች ጦሩን ለማወያየት ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ ስፍራው አቅንተው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል። ጦሩ መስዋዕትነት እየከፈለ በተደጋጋሚ የተቆጣጠረውን ቦታ እንዲለቅ ትዕዛዝ ሲቀበል መቆየቱ ሌላው የቅሬታው መነሻ ሲሆን በሶማሌ ያለው የሰላም አስከባሪ ሃይል ይህንኑ ነቅፎ መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል። በህወሃት የሚመሩት የኢህአዴግ ባለስልጣናት በሶማሌ ስለተገደሉት ወገኖች መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸው፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ይህንን አክርረው አለመጠየቃቸው፣ ላለፉት አምስት ዓመታት 99.6 በመቶ ህወሃት የነገሰበት ማኅበርም (ፓርላማ) ለይስሙላ እንኳን ጥያቄ አቅርቦ እንደማያውቅ በርካቶች የሚተቹበት አገራዊ ጉዳይ ነው።

ከጎልጉል የተወሰደ

torsdag 17. september 2015

ምኞትና ተግባር ምንና ምን ናቸው? ርዕዮት አለሙ

በአዲሱ አመት ዋዜማ የፖለቲካ እስረኞችን ለመጠየቅ ወደ ቂሊንጦ እስርቤት ከእህቴ ጋር ሄጄ ነበር፡፡ ስማችንን እና የምንጠይቃቸዉን እስረኞች ስም ካስመዘገብን በኋላ መታወቂያችን አሳይተን ወደዉስጥ ልንገባ ስንል መታወቂያዉን የምትመለከተዉ ፖሊስ ስማችንን ካነበበች በኋላ "ቆይ ቆይ የእናንተማ መጠየቅ አለበት" አለችንና መታወቂያችንን ይዛ ከበር መለሰችን፡፡ ከበሩ አጠገብ በሚገኝ ጎብኝዎች ወረፋ በሚጠብቁበት የእንጨት መቀመጫ ላይ አረፍ እንዳልን በሃሳብ ላይ ታቹን ማለት ጀመርኩ፡፡ እንድንገባ ይፈቅዱልን ይሆን ወይስ የቃሊቲዎቹ እንዳደረጉት "ፍቃድ የላችሁም" የሚል አስቂኝና አናዳጅ መልስ በመስጠት ይመልሱን ይሆን? ለሚለዉ ጥያቄ መልሱ እኔዉ ጋር ያለ ይመስል አጎንብሼ ማሰቤን ቀጠልኩ፡፡ ቀና ስል ከፊት ለፊቴ "ማረሚያ ቤቱ" ለእስረኛ ቤተሰቦች መልካም ምኞቱን የገለፀበት ወረቀት ተለጥፎ ተመለከትኩ፡፡ ከአራት አመታት በላይ በመኖር የእስርቤቶቹን አሰራር አዉቀዋለሁና ተመሳሳይ የመልካም ምኞት መግለጫ የያዘ ወረቀት ለእስረኛዉም ተለጥፎ እንደሚሆን አልተጠራጠርኩም፡፡ ሰላም እየነሳ ሰላም "የሚመኝ"፣ ህክምና እየከለከለ ጤንነትን "የሚመኝ"፣ የሚዋደዱ ሰዎችን ከሽቦ ወዲያና ወዲህ ሆነዉ እንኳን እንዳይተያዩ እየከለከለ ፍቅርን "የሚመኝ" . . .ተቋም ! አንድ ፖሊስ ወደኛ እየቀረበ ሲመጣ ሀሳቤ ተቋረጠ፡፡ መታወቂያዬን እየመለሰልኝ መግባት እንደማልችል ነገረኝ በኋላ ለእህቴም ተቀራራቢ መልስ በመስጠት መታወቂያዋን መለሰላት፡፡ ለምን ለሚለዉ ጥያቄያችን "አላዉቅም፡፡ የተወሰነውን ንገር ተብዬ ነው" የሚል ምላሽ ሰጠን፡፡ ምን አይነት አምባገነንነት ነው? እስር ቤት እያለሁ በሌሎች የመጎብኘት መብቴን የነፈገው ስርዐት ዛሬ ደግሞ የጠያቂነት መብቴን እየነፈገው ነው፡፡ ሙሉውን ቀን ሊባል በሚችል መልኩ ስለፖለቲካ አሳሪዎቻችን ጉዳይ እያሰብኩ ስብሰለሰል ዋልኩ፡፡ የእኔና የሌሎች በርካቶች መብሰልሰል ምክንያት የሆኑት የኢህአዴግ ባለስልጣናት ደግሞ በአሉን ምክንያት በማድረግ ፍትህ እያዛቡበተ፣ እያሰሩትና እየገደሉት ላሉት ህዝብ የመልካም ምኞት መግለጫቸዉን ሲያዥጎደጉዱለት ዋሉ፡፡ ይህንን የኢህአዴግ ምኞትና ተግባር መራራቅ እያሰብኩ እያለሁ "ኢህአዲግን ለመለወጥ የምንፈልግ ሰዎች ምኞትና ተግባርስ ምን ይመስላል? " የሚል ጥያቄ ሽው አለብኝ፡፡ ጥያቄው በርካታ መልሶች ቢኖሩትም በዚህ ጽሁፍ ለማቅረብ የመረጥኳቸው ግን ሁለቱን ብቻ ነው፡፡ አጉል ህልመኞች በዚህ ስርዓት ተጠቃሚ በመሆናቸው ብቻ የሌሎችን ወገኖቻቸውንና የሀገርን ጉዳት ማየት ካልቻሉ ወይም ካልፈለጉ ሆዳሞችና በህወሓት የዘረኝነት መርዝ ከተበከሉ ጥቂቶች በቀር የኢህአዴግን መሰንበት የሚፈልግ ዜጋ ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች የማገኛቸዉ ሰዎች ምኞትም የስርዓት ለውጥን ማየት ነው፡፡ ነገር ግን "እነዚህ ሁሉ ሰዎች የሚፈልጉትን ለውጥ ለማየት ምን አይነት አስተዋፅኦ እያደረጉ ነው?" ብለን ብንጠይቅ የምናገኘው ምላሽ አስደሳች አይደለም፡፡ አንዳንድ ለዉጥ ፈላጊዎች ቁጭ ብሎ ከመመኘት በቀር ለለዉጡ መምጣት የሚያደርጉት ምንም ነገር የለም፡፡ ለምን አንዳች ነገር እንደማያደርጉ ስትጠይቋቸው ከምታገኟቸዉ መልሶች መሃከል "እነዚህን መዥገሮች እሱ ይንቀላቸዉ እንጂ በሰው ሃይልማ የሚሆን አይደለም፤ ህዝቡን ከፋፍለውታል እኮ ምን ማድረግ ይቻላል? . . ." የሚሉት ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ሰዎች ምንም እንዳይሰሩ ያደረጋቸዉ ትልቁን ምክንያት ጠጋ ብላችሁ ስትመረምሩ ግን ፍርሃት ሆኖ ታገኙታላችሁ፡፡ ፕ/ር መሳይ ከበደ "The Impasse of Fear in Ethiopia and the Necessity of Comprehensive struggle ” በተሰኘ ፅሑፋቸዉ እንዳስቀመጡት ፍርሃት የጨመደደው ህዝብ ሁሌም ምንም ላለማድረጉ የሚያቀርባቸው በርካታ ምክንያቶች ይኖሩታል፡፡ ሌሎቹ ለዉጥ ፈላጊዎች ደግሞ ለዉጥ ሊያመጡ የሚችሉ እንቅስቃሴዎቸን በማድረግ ረገድ ከላይኞቹ የተሻሉ ቢሆኑም የጀመሩትን መጨረስ ግን የማይሆንላቸው ናቸው፡፡ እያደረጉ በነበረዉ እንቅስቃሴ ሳቢያ አንዳች ችግር ሲደርስባቸው ከመንገዳቸው ይወጣሉ፡፡ "በዚህኛው አመተምህረት በተደረገው ምርጫ ሳቢያ ለእስር ተዳርጌ ነበር፤ በዛኛው ወቅት በተደረገው ሰልፍ ላይ ተገኝቼ ተደብድቤያለሁ" ማለት ይቀናቸዋል፡፡ አሁንስ? ስትሏቸው ግን መልሳቸው "ጎመን በጤና" ነው፡፡ እንደነዚህ አይነቶቹ ሰዎች መጀመሪያዉኑ እየታገሉት የነበረውን መንግስት ግፈኝነት በሚገባ ያወቁት አይመስሉም፡፡ የቆረጡ ለዉጥ ፈላጊዎች እነዚህኞቹ አስቀድሞ ከተጠቀሱት ጋር የለዉጥ ፍላጎታቸው ቢያመሳስላቸውም ለውጥን ለማምጣት የሚያደርጉት እንቅስቃሴ መኖሩና ቁርጠኝነታቸው ደግሞ የተለዩ ያደርጋቸዋል፡፡ "እሱ ያመጣዉን እሱ እስኪመልሰው" በማለት እጃቸውን አጣጥፈው አይቀመጡም፡፡ ለለውጡ እዉን መሆን የሚችሉትን ሁሉ ያዋጣሉ፡፡ ከነዚህ ሰዎች መሀከል በግንባር ቀደምትነት ሊጠቀስ የሚገባው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን መዉሰድ ይቻላል፡፡ እስክንድር ለለዉጡ ያለውን ሁሉ እየከፈለ ያለ ሰው ነው፡፡ ወደስምንት ጊዜ ያህል ሲታሰርና ሲፈታ፣ የመፃፍ መብቱን ሲገፈፍ፣ ሲደበደብ፣ ንብረቱ ሲወረስና ከሚወዳት ባለቤቱና ልጁ ጋር በአካል መለያየት ግድ ሲለዉ ሁሉ በአላማው ከመጽናት ውጭ ለአፍታ እንኳን ሸብረክ ሲል አልታየም፡፡ እስክንድርና መሰሎቹ ዲሞክራሲ እንዲሰፍንና ነፃነት እንዲገኝ ካስፈለገ ከምኞት ባለፈ ስራና መስዕዋትነት እንደሚጠይቅ ገብቷቸዋል፡፡ ለገባቸው እውነት ደግሞ እየኖሩ ነው፡፡ እነ እስክንድር ይሄን ሁሉ መስዕዋትነት ሲከፍሉ ታዲያ ሁኔታው ያማያማቸው ሆኖ አይደለም፡፡ ህመሙን ጥርሳቸውን ነክሰው እየቻሉ እንጂ! አቶ ኤፍሬም ማዴቦ "ከዊሃ እስከ ኦምሃጀር-አንድ ሰሞን ከአርበኞች ጋር" በሚል ርዕስ በቅርቡ ባስነበቡን ጽሑፋቸዉ የአርበኞች ግንቦት 7 ጦርን ለመቀላቀል ከአሜሪካን ሀገር ከተደላደለ ኑሮዋቸው ተነስተው ሲሄዱ ይሰማቸው የነበረዉን ከሚወዱት ልጃቸው የመለየት ህመም በዉብ አገላላፅ ተርከዉልናል፡፡ አቶ ኤፍሬም አውሮፕላን ማረፊያ ድረስ ሊሸኛቸው የመጣዉን የ17 አመት ልጃቸውን ሲሰናበቱ "ልጄ ይሄን ማድረግ አልፈልግም ነገር ግን ማድረግ አለብኝ" ያሉት ፊታቸው በእንባ እየታጠበ ነበር፡፡ የማይፈልጉትን ነገር ለማድረግ እራሳቸዉን ያስገደዱበትን ምክንያት የገለጹት "የምወደውን አንድ ልጄንና ጥሩ ስራዬን ደህና ሁኑ ብዬ በረሃ የገባሁት ሃገሬ ዉስጥ ፍትህ፣ ነፃነት፣ እኩልነትና ዲሞክራሲ አብቦ ለማየት ነው" በማለት ነው፡፡ ጋዜጠኛ እስክንድርና አቶ ኤፍሬም ምንም እንኳን ለውጥን ለማምጣት የሚሄዱበት መንገድ ለየቅል ቢሆንም ሁለቱም ግን ለለውጡ ያላቸውን ሁሉ ለመስጠት ተዘጋጅተዋል፡፡ አንደኛቸው ለውጡ ግድ ብሎአቸው ቤታቸው እስርቤት ሲሆን ሌላኛቸው ዱርቤቴ ብለዋል፡፡ ሁለቱም ከሚወዷቸው ወንዶች ልጆቻቸው ጋር ተለያይተዋል፡፡ ሁለቱም ለውጥ በምኞት ብቻ እንደማይመጣ ያውቃሉና እራሳቸው ሄደው ይገናኙት ዘንድ በተለያየ መንገድም ቢሆን በጉዞ ላይ ናቸው፡፡ በመጨረሻም . . . በኢትዮጵያ እኩልነት ዴሞክራሲ ነፃነትና ፍትህ እንዲሰፍን የምንመኝ ሁላችን ከቀን ህልማችን መንቃትና ምኞቶቻችንን ወደ ተግባር ለመለወጥ መንቀሳቀስ ያስፈልገናል፡፡ ከመንቀሳቀስ ያገደን ፍርሃታችን ከሆነ በቀደመው ንዑስርዕስ ስር የጠቀስኩት የፕ/ር መሳይ ጽሑፍ ፍርሃትን ለመዋጋት የሚያስቀምጠው አንድ መፍትሄ አለ፡፡ ድርጊት! ራሳችንን ለፈሪነት የተመደብን አድርገን የምንቆጥርና በሌሎች ደፋርነት መንፈሳዊ ቅናት የሚያድርብን ሰዎች ካለን ፕ/ሩ የጠቀሱት የፈላስፋው አርስቶትል ሃሳብ ሳይጠቅመን አይቀርም፡፡ አርስቶትል "ጀግና ለመሆን ጀግንነትን መለማመድ ያስፈልጋል" ይለናል፡፡ ለአርስቶትል ድፍረት እንደሌሎቹ የሞራል እሴቶች ሁሉ አብሮን የሚወለድ እምቅ ሃይል ሲሆን እውን ለመሆንና ለመዳበር እንዴሎቹ እሴቶች ሁሉ ልምምድ ያስፈልገዋል፡፡ አስፈላጊዉ ጥንቃቄ እንደዳለ ሆኖ እስኪ እስከዛሬ ያላደረግነዉን አንድ ድፍረት የተሞላበት ድርጊት እናድርግ፡፡ ፕ/ሩ እንደሚሉንና እኔም እንደማምነው ድርጊት ስኬትን ያመጣል፡፡ ስኬቱ የቱንም ያህል ትንሽ ቢሆን በራስ መተማመንን ይወልዳል፡፡ በራስ በተማመን ሲኖር ደግሞ ፍርሃት ይጠፋል ወይም ችግር ሊሆን በማይችልበት ደረጃ ዝቅ ይላል፡፡ ከፍርሃታችን ወጥተን እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ሳለን ከኢህአዴግ በሚወረወርብን ዱላ ተሰብረን ከመንገዳችን ላለመውጣት ደግሞ የገዢዉን ፓርቲ ማንነት ጠንቅቆ ማወቅና ቢያንስ የስነልቦና ዝግጅት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ለማንጠብቀው ነገር አንዘጋጅም፡፡ ያልተዘጋጀንበት ነገር ደግሞ ሁሌም ይጥለናል፡፡ በመሆኑም የምንታገለው ስርዓት ስልጣኑን ላለማጣት የቱንም አይነት ጭካኔ የተሞላው እርምጃ እንደሚወስድ ማወቅና ለዛም እራስን ማዘጋጀት ግድ ይላል፡፡ ደግሞስ ኢህአዴግ ምን ሊያደርገን ይችላል? ሊያደርገን የሚችለው ሁሉ አስቀድሞም ከአፈር በታች እንዲዉል የተወሰነበት ስጋችን ላይ አይደለምን? መልካም አዲስ አመት! መስከረም 3/ 2008 – Ethiomedia.com – September 14, 2015
Source Ethiomedia.com

fredag 4. september 2015

ሀብታሙ አያሌው ቂሊንጦ እስር ቤት ላይ ያቀረበው አቤቱታ ውድቅ ተደረገ



በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
 አቶ ሀብታሙ አያሌው ነሀሴ 14/2007 ዓ.ም ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከተከሰሰበት የሽብር ወንጀል ነጻ ነው በማለት ከእስር እንዲፈታ የሰጠው ትዕዛዝ ተከብሮ እንዲፈታ ትዕዛዝ እንዲሰጥለት ለከፍተኛ ፍርድ ቤት ተረኛ ችሎት ያቀረበው አቤቱታ ውድቅ ተደርጓል፡፡ ዛሬ ነሀሴ 29/2007 ዓ.ም ልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ተረኛ ችሎት የቀረቡት አቶ ሀብታሙ አያሌው እና መልስ እንዲሰጥ የተጠራው የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ተወካዮች ሲሆኑ፣ የእስር ቤቱ የእስረኛ አስተዳደር ኃላፊ ሱፐር ኢንቴንደንት ጣዕመ ደምሴ አቶ ሀብታሙ አያሌውን ለምን ከእስር እንዳልለቀቁ አስረድተዋል፡፡ ኃላፊውእንደሚሉት አቶ ሀብታሙ ከቂሊንጦ እስር ቤት ያልተፈታበት ምክንያት እስር ቤቱ ከአቃቤ ህግ ይግባኝ እንደተጠየቀበት እና ይህን ተከትሎ ተያይዞ ከጠቅላይ ፍርድ ቤት የተጻፈ የእግድ ትዕዛዝ ስለደረሳቸው ነው፡፡ ሱፐር ኢንቴንደንት ጣዕመ ደምሴ እንደገለጹት የመፈቻ ደብዳቤው እና የእግድ ትዕዛዙ የደረሳቸው ነሀሴ 15/2007 ዓ.ም ሲሆን፣ አቶ ሀብታሙ ግን ከእስር መፈቻ ትዕዛዙ የተጻፈለት ከከፍተኛው ፍርድ ቤት ነጻ ናችሁ የሚል ብይን በተሰጠበት ዕለት፣ ማለትም ነሀሴ 14/2007 ዓ.ም ነበር፡፡ በመሆኑም አቶ ሀብታሙ የማስፈቻ ደብዳቤው እንደተጻፈለት ከእስር ሊለቀቅ ይገባ ነበር፡፡ በእርግጥም የማስፈቻ ደብዳቤው በ14/2007 ዓ.ም እንደተጻፈ ነገረ ኢትዮጵያ ማረጋገጥ ችላለች፡፡ በሌላ በኩል አቶ ሀብታሙ አያሌው ይግባኝ እንደተጠየቀበትና የእግድ ትዕዛዝ ለቂሊንጦ እንደተጻፈ በወቅቱ በደብዳቤ ጭምር መረጃ የጠየቀ ቢሆንም እንዳልተነገረው ለተረኛ ችሎቱ አስረድቷል፡፡ በዚህም ቤተሰቦቹ ለእንግልት፣ አቶ ሀብታሙ ደግሞ ለሞራል ጉዳት መዳረጋቸውን ተናግሯል፡፡ ቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ግን ይህን ባለመቀበል በጊዜው መረጃ መስጠቱን ይከራከራል፡፡ ተረኛ ችሎቱ የቀረበለትን አቤቱታ እና የአስተዳደሩን መልስ ከሰማ በኋላ ቂሊንጦ እስር ቤት ከጠቅላይ ፍርድ ቤት የደረሰውን ትዕዛዝ እንዳስፈጸመ በመጥቀስ ትክክለኛ ነው ሲል በይኗል፡፡ በመሆኑም አቶ ሀብታሙ አያሌው በእስር ቆይቶ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሚሰጠውን ብይን እንዲጠብቅ ታዝዟል፡፡ አቶ ሀብታሙ የተረኛ ችሎቱን ብይን ከሰማ በኋላ ‹‹ይህ ችሎት ታሪካዊ ስህተት እየሰራ ነው፤ የውሳኔ ግልባጩ ይሰጠኝና የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያውቀው አደርጋለሁ›› ሲል ተናግሯል፡፡ አቶ ሀብታሙ አያሌው ከሌሎች አራት ተከሳሾች ጋር መስከረም 21/2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ - See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/10187#sthash.32fx6TF6.dpuf

torsdag 3. september 2015

በእስር ላይ የሚገኙ ሦስት የሰማያዊ አባላት በዓለም ላይ ከተመረጡ 20 የፖለቲካ እስረኞች መካከል ተካተቱ


 ሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪዎች የአንድ ወር ዘመቻ ያደርጉላቸዋል በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር በአሜሪካ መንግስት ኦፊሳላዊ ድረ ገጽ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ጉዳይ አስተባባሪነት በዓለም ላይ ለተመረጡ 20 ሴት የፖለቲካ እስረኞች ለአንድ ወር የሚቆይ ዘመቻና ማስታወሻ ሊደረግላቸው ነው፡፡ ከ20ዎቹ ሴት የፖለቲካ እስረኞች መካከል ሦስቱ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ፣ ሁሉም የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፡፡ ከዛሬ 20 አመት በፊት ሴቶችን ለማብቃት፣ የጾታ እኩልነትን ለማስፈን እና የልጃ ገረዶችን ሰብዓዊ መብት ለማስጠበቅ የቤጂንግ መርሃ ጉዞ ተቀምጦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእነዚህ 20 አመታት ልክ ከዓለም ሀገራት በፖለቲካ እስረኝነታቸው የተመረጡ 20 ሴት እስረኞችን ለማሰብ የሚደረገው ዘመቻ መነሻው ይህ መርሃ ጉዞ ነው፡፡ በዚህ መሰረት ከኢትዮጵያ ብሌን መስፍን፣ ንግስት ወንዲፍራው እና ሜሮን አለማየሁ የተካተቱ ሲሆን ከቻይና እንዲሁ ሦስት ሴት የፖለቲካ እስረኞች ተመርጠው ይታወሳሉ፡፡ ከብዙ ሴት የፖለቲካ እስረኞች መካከል እነዚህ ጥቂቶች መሆናቸውን የጠቀሰው ድረ ገጹ በመስከረም ወር ‹‹ሴቶችን አብቋቸው፣ አትሰሯቸው!›› በሚል መርህ ዘመቻው ይደረጋል፡፡ በዚህም መንግስታት ሴቶችን በፖለቲካ አመለካከታቸው ማሰር አቁመው ማብቃት ላይ እንዲያተኩሩ መልዕክት ይተላለፍበታል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ዘመቻው ለታሳሪ ቤተሰቦችና ለራሳቸው ለታሳሪዎች ብቻቸውን እንዳልሆኑና እንዳልተዘነጉ ለማሳየት ታስቦ እንደሚካሄድ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ የሰጡት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፣ በኢትዮጵያ ሦስት ሴት የፖለቲካ እስረኞች በዚህ ደረጃ መጠቀሳቸው በሀገራችን ያለውን ስርዓት ዓለም እንደተረዳውና ኢትዮጵያ በመጥፎ እንድትነሳ እያደረጋት መሆኑን ያሳያል ብለዋል፡፡ ዘመቻው እንዲደረግላቸው ከተመረጡት መካከል ከኢትዮጵያና ቻይና ሶስት ሶስት፣ ከቬትናም፣ አዘርባጃንና በርማ ሁለት ሁለት እንዲሁም ከኢራን፣ ግብፅ፣ ኤርትራ፣ ኡዝቤኪስታን፣ ቬንዞዌላ፣ ሶሪያ፣ ሩሲያ/ዩክሬንና ሰሜን ኮሪያ አንድ አንድ ሴት የህሊና እስረኞች ናቸው፡፡ - See more at:
http://www.zehabesha.com/amharic/archives/46394#sthash.c0DUxD3n.dpuf

tirsdag 1. september 2015

ቤኒሻንጉል ክልል በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ግድያ ተፈጸመባቸው

ethiopians-illegally-deported-from-benshangul-region-to-amhara-region-finote-selam-town-photo-addis-admass
 
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሚገኙ የአማራ ተወላጆች ላይ የተቀነባበረ ጥቃት መሰንዘሩን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገለጹ። ባለፈው ሚያዚያ ወር መጨረሻ ተፈጸመ በተባለው በዚሁ ጥቃት፣ ከ80 በላይ ሰዎች መገደላቸውንና በአንድ ቀበሌ ውስጥ የሚገኙ አማሮች ሙሉ በሙሉ የጥቃቱ ሰለባ መሆናቸውን ዕማኞች ለኢሳት ገልጸዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወንበራ ወረዳ መልካ ቀበሌ ከሶስት ወራት በፊት በተፈጸመው በዚሁ ጥቃት 84 ሰዎች መገደላቸውን የገለጹት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ግድያውም በጦር መሳሪያና በስለት ጭምር የታገዘ መሆኑን አስረድተዋል። ለቀናት አማሮች የሚደርስላቸው በማጣታቸው የተረፉት ንብረታቸውን ጥለው መሸሻቸውን ገልጸዋል።
ሚያዚያ 27 እና 28 ለሁለት ቀናት በወንበራ ወረዳ መልካ ቀበሌ ለቀጠለው ጥቃት መነሻው አንድ የአካባቢው ተወላጅ ባልታወቁ ሰዎች ተገደሎ መገኘቱ እንደሆነም ተመልክቷል።
በአማሮች ላይ በአካባቢው ባለስልጣናት ግፊትና ድጋፍ ለተቀነባበረውና ለቀጠለው ጥቃት የሚደርስ አካል በመታጣቱ፣ ሰለባዎቹ ለቀናት አደጋውን ሲጋፈጡ መቆየታቸውንም መረዳት ተችሏል።
ኢሳት ያነጋገራቸው ሁለት የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለጹት የሟቾቹ አስከሬን የተሰበሰበው የመከላከያ ሰራዊት አባላት ከቀናት በኋላ ወደስፍራው ሲደርሱ ነው።
ጥቃቱን በማድረስ የተጠረጠሩ 10 ያህል ሰዎች የተያዙ ቢሆንም፣ ድርጊቱን በማቀነባበርና በመምራት ተሳታፊ የሆኑ ባለስልጣናት አለመጠየቃቸውን መረዳት ተችሏል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወንበራ ወረዳ መልካ ቀበሌ የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች በአብዛኛው ሲገደሉ፣ የቀሩት በመሸሻቸው በአሁኑ ወቅት በቀበሌው አንድም የአማራ ተወላጅ እንደማይኖር ለኢሳት ምስክርነታቸውን የሰጡ ወገኖች ገልጸዋል።
Source:: Ethsat
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/10083#sthash.3JXrU37K.dpuf

በጀኔራል ሳሞራ የኑስ እየተመራ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው ስብሰባ ያለመፍትሄ ተበተነ

September 1,2015
samora yunus
በጀኔራል ሳሞራ የኑስ እየተመራ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የመከላከያ  ከፍተኛ አዛዦች ግምገማዊ ስብሰባ ያለመፍትሄ መበተኑን ለማወቅ ተችሏል።በመረጃው መሰረት- በአዲስ አበባ ከተማ በጀኔራል ሳሞራ የኑስ የተመራው የገዥው መንግስት ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ የመከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ አዛዦች ከነሃሴ 12 ቀን 2007 ዓ/ም ጀምሮ ሲካሄድ እንደቆየ የገለፀው መረጃው፤ የስብሰባው አጀንዳም መንግስት አዲስ የመከላከያ ሰራዊት አሰልጥኖ ይለቃል ወደ እናንተ ሲደርስ ግን በርካታው ሰራዊት ይጠፋል ምክንያቱ ምንድንነው? ስራችሁ ምንድንነው? የሚሉና ሌሎችም በመድረክ መሪው በሳሞራ የኑስ የቀረቡ ሲሆን በርካታዎቹ በተቃውሞ ድምፅ ስለተቃወሙት በመካከላቸው ልዩነት ተፈጥሮ ስብሰባው ያለ ፍሬ ነገር እንደተበተነ ለማወቅ ተችሏል።

መረጃው ጨምሮም- ግምገማው በከፍተኛ አዛዦች ዘንድ መረዳዳት ያልነበረው ስብሰባ እስከ ታች እዞች የወረደ ሲሆን በተለይ በሰሜን እዝ ከሚገኙ ሬጂመንቶች በሚጠናቀቀው አመት ብቻ በረከት ያለ ቁጥር ያላቸው ወታደሮች በመጥፋታቸው ዋና መነጋገሪያ አጀንዳ በመሆኑ አንዳንድ አዛዦች ከስራቸው ታግደው በመቐለ ስታፍ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል።

søndag 30. august 2015

ጎሳን ለይቶ የሚደረግ ጥቃትን ለማስወገድ መሰረታዊ ለውጥ ያሻል

 shengo 
አንድ መንግስት ልማታዊ ሊባል የሚችለው የሚመራውን ሕዝብ ከዃላ ቀርነትና ከድህነት አሮንቓ መንጥቆ ሲያወጣ፣የህዝቡን አንድነትና መልካም ግንኙነት ሲያጠናክር፣የአገርን ብሔራዊ ጥቅምና ዳር ድንበር ሲያስከብር ነው።
ሕዝብ በኑሮ ክብደት የሚሰቃይበትና የበይ ተመልካች በሆነበት፣ወጣቱ ተስፋ ቆርጦ ለስደት ሲዳረግና እግረመንገዱን ለተለያዩ አደጋዎች የሚጋለጥበት፣የጎሳ ስሜት ነግሶ አንዱ ሌላውን እንዲጠላና ሰላም እንዲናጋ፣ዜጋ ለዘመናት ከኖረበት ቦታና መሬት በሃይል እየተፈናቀለ እንዲበታተን የሚያደርግ ስርዓት ያሰፈነ ቡድን የሚመራው መንግስት ጥፋታዊ እንጂ ልማታዊ ተብሎ ሊጠራ አይገባውም።
የሕዝቡን መብት ገፎ፣የአገሩን ሃብትና ንብረት፣ለም መሬት ጭምር ለባዕዳን አሳልፎ እየሰጠ፣እየሸጠና ተባብሮ እየመዘበረ በውጭ አገር ባንክ የሚያካብት ቡድን ስልጣን ላይ ባለበት አገር ውስጥ ልማታዊ መንግስት አለ ብሎ ማመን ቀርቶ መናገሩ የስህተት ስህተት ነው።
ብሔራዊ ስሜትና የአገር ፍቅር፣ለራሱ ሕዝብ አክብሮት የሌለው ቡድን ኪራይ የሚሰበስብባቸው ታላላቅ ሕንጻዎች ስለሰራ፣የውጭ አገር ተባባሪዎቹን ለማስተናገድና ለመሳብ ሆቴሎችንና መንገዶችን በመገንባቱ ብቻ ልማታዊ ነው ብሎ መቀበልና ማስተጋባት ስለልማት ሁለንተናዊነት ሊኖር የሚገባውን ግንዛቤ ይጻረራል።ልማት በአጭሩ ሲተረጎም የሕዝብ ኑሮ መሻሻልን፣የሰብአዊ መብት መከበርን፣የዜጎችን ደህንነትና ሰላማዊ ኑሮ ዋስትና መኖርን፣የዴሞክራሲና የዜጎች መብት መረጋገጣቸውን ማሳየት ይኖርበታል።ሕዝብ በአገሩ ጉዳይ የማይመክርበት፣የማይወስንበት ሁኔታ ካለ ትርጉም የሚሰጥ ልማት ሊኖር አይችልም።ልማት ማለት የትቂቶችን ከርስ ሞልቶ ማደር ብቻ ሳይሆን በህዝብ ውስጥ የመንፈስ እርካታም ጭምር ሲኖር ነው።የአገር ዜግነትና ባለቤትነትም በተግባር ሲገለጽ ነው።
ይህ ከዚህ በላይ በጥቅሉ የቀረበው መንደርደሪያ የህወሃት/ኢሕአዴግን ፖሊሲወች ምንነት ለመግለጽ ከሚያስችሉት አንኳር ነጥቦች ጥቂቱ ሲሆን፣ሰሞኑን ደግሞ አንድ መንግስት አለ ተብሎ በሚገመትበት አገር ቀርቶ ወራሪ ጠላት በሚያስተዳድረው አገር ውስጥ እንኳን ይሆናል ተብሎ የማይጠበቅ ድርጊት፣ሰው ሰውን ቀቅሎ የሚበላበት ፈቃድና ድርጊት መፈጠሩ የስርዓቱን ምንነት በጉልህ ያሳያል።
ዛሬ በጉሙዝ ክልል ውስጥ በአማራነታቸው ተቀቅለው የተበሉት ወገኖች እንደ ወንጀል የተቆጠረባቸው ነገር ቢኖር በኢትዮጵያዊነታቸው የሚያምኑና ሁሉንም ማህበረሰብ እንደራሳቸው ቆጥረው አብረው ለመኖር መወሰናቸውና መኖራቸው ነው።
በጉሙዝ ክልል ውስጥ ለተፈጸመው ኢሰብአዊ ድርጊት ሀገርን አሰተዳድራለሁ የሌለው ክፍል በቴሎቪዥን መስኮት ቀርቦ የአዞ እንባ ከማፍሰስ አልፎ ድርጊቱን የፈጸሙትን ሁሉ መንጥሮ እያወጣ በይፋ ለህግ ማቅረብ  ችግሩን በመሰረታዊነት ለመፍታት ደግሞ ከሁሉም ባለድርሻወች ጋር መወያየት ይኖርበታል፣ጉዳት የደረሰባቸውንም ወገኖቹን ለመካስና ተመሳሳይ አውሬያዊ አድራጎት እንዳይፈጸምባቸው ዋስትና ሊሰጣቸው ይገባል። በተጨማሪም ስርአቱ ሁሉም ዜጎች በሁሉም የኢትዮጵያ ምድር በክልሉ አስተዳደር ውስጥ ሙሉ በሙሉ እንዲሳተፉ መብታቸውን ማክበርና ሁኔታውን ማመቻቸት ይኖርበታል።
ሸንጎ የአማራው ማህበረሰብን ጨምሮ በሁሉም ኢትዮጵያዊ  ላይ በተደጋጋሚ የሚደርሰውን ግፍና መከራ ሲያጋልጥና ሲያወግዝ ቆይቷል። ላለፉት ግፎች ምንም አይነት ሕጋዊና መሰረታዊ መፍትሔ ስላልተገኘላቸው አሁን የደረሰው ዘግናኝና አሳፋሪ ድርጊት እንዲከሰት ዕድልና በሩን የከፈተው በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ፖሊሲና ተግባር እንደሆነ በማመን ከማጋለጥ በላይ በዓለም አቀፍ ሕጋዊና  ሰብዓዊ መብት መድረኮች ላይ ጉዳዩን ለማቅረብ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር ለመተባበር ዝግጁ መሆኑን እየገለጸ በውጭ አገርና በአገር ውስጥ የሚገኙት ድርጅቶችና የሃይማኖት ተቋማት ድርጊቱን በማውገዝ ከሚጠቁት ኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ጎን እንዲሰለፍና አስፈላጊውን ዕርዳታና ድጋፍ እንዲለግሳቸው ለደህንነታቸውም ዋስትና በሚሰጠው መንገድ ሁሉ እንዲተባበር ጥሪ ያደርጋል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ

torsdag 27. august 2015

መልዕክት በድሆች ድህነት ለመክበር መሯሯጥ ላይ ላሉ የዲያስፓራ ማኅበረሰብ አባላት !


August 27, 2015
def-thumbየግል ኑሮን ለማደላደል ሲባል የወያኔ አባል መሆን “ወይን ለመኖር” የሚል ስያሜ ከተሰጠው ዓመታት ተቆጥሯል። “ወይን ለመኖር” ዜጎች ነፃነታቸውን ለጥቅም አሳልፈው የሚሸጡበት፤ የሰው ልጅ ክብር የሚዋረድበት ገበያ ነው። በወይን ለመኖር “የገበያ ህግ” መሠረት እያንዳንዱ ዜጋ ሊያገኘው መብቱ የሆነውን አገልግሎት እንዲያገኝ የህወሓት፣ የብአዴን፣ የኦህዴግ፣ የደህዴግ፣ የአብዴፓ፣ የቤጉህዴፓ፣ የጋህአዴን፣ የሀብሊ ወይም የኢሶዴፓ አባል መሆን፤ አልያም መደገፍ ግዴታ ነው። እነዚህ ሁሉ ድርጅቶች የህወሓት ተቀጽላ ወያኔዎች ናቸው። የእነዚህ ድርጅቶች አባል ወይም ደጋፊ ያልሆነ እንኳስ የመንግሥት አገልግሎት ሊያገኝ ጥሮ ግሮ ያፈራውንም ይነጠቃል።
በዚህም ምክንያት፣ በገጠር ያለው አርሶ አደር ቁራጭ የእርሻ መሬት፣ የግብርና ባለሙያዎች የምክር እገዛ፣ የማዳበሪያና ዘር ግዢ፣ ብድር ወይም እርዳታ ለማግኘት በአካባቢው ባለ የወያኔ ድርጅት አባልነት መመዝገብ፤ አንድ ለአምስት መደራጀት እና የወያኔን የስልጣን እድሜ የሚያራዝሙ ነገሮችን መሥራት ይጠበቅበታል። በከተሞች ውስጥም ሥራ ለመቀጠር፣ ለደረጃ እድገት፣ የመኖሪያ ቤት (ኮንዶሚንየም) ለመግዛት ሲባል መወየን አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ሆኗል:: በንግዱም ዘርፍ የንግድ ፈቃድ፣ የሥራ ቦታ እና የባንክ ብድር ለማግኝት፣ የመንግሥት ጨረታዎችን ለማሸነፍ፣ ከጉምሩክ እቃ ለማስለቀቅ፣ የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት መወየን ግዴታ ነው።
“ወይን ለመኖር” የኢትዮጵያን ሕዝብ ያዋረደ፤ ለትውልድ የሚተርፍ የማኅበራዊ ስነልቦና ኪሳራ ያደረሰ እና ደካማውን ወያኔን ጠንካራ በማስመሰል በሕዝብ የትግል መንፈስ ውስጥ ፍርሃትን የረጨ መሆኑ ግንዛቤ እየዳበረ በመጣ መጠን እየቀነሰ የመጣ ክስተት ነው። በአሁኑ ሰዓት ከቀድሞው እጅግ በተሻለ ኢትዮጵያ ውስጥ የምንገኝ ኢትዮጵያዊያን ራሳችንን ከህወሓት ባርነት እያላቀቅን ምሬታችንን በግልጽ መናገር የጀመርንበት ወቅት ነው፤ ከዚያም አልፎ የህቡዕ ተግባራዊ የትግል እንቅስቃዎችን ማድረግ ደረጃ ላይ ደርሰናል።
አገር ውስጥ እየተዋረደ የመጣው “ወይን ለመኖር” በአገዛዙ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካይነት በውጭ አገራት ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን (ዲያስፓራ) መካከል ነፃነታቸውን በጥቅም የሚለውጡ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያንን ፍለጋ ተሠማርቷል። አገዛዙ ተስፋ ያደረገው ያህል ባይሆንም ጥረቱ የተወሰነ ውጤት እያስገኘለት ነው። በጥቅማ ጥቅም እየደለለ ካመጣቸው ውስጥ በስርዓቱ ብልሹነት ያዘኑና የተሰማቸውን በግልጽ የተናገሩ መኖራቸው የሚያስደስትና የሚያበረታታ ቢሆንም ከመንደር ካድሬዎች ባነሰ ተለማማጮችና አጎብዳጆች በማየታችን ተሸማቀናል። ኢትዮጵያ ውስጥ ካለነው አብዛኛው ሕዝብ አንፃር ሲታይ በተሻለ የኑሮ ደረጃ ላይ ከሚገኙት ዲያስፓራዎች መካከልም ነፃነታቸውን በጥቅም ለመለወጥ የሚፈቅዱ መገኘታቸው አሳዛኝ ነው። እነዚህ ክብራቸውን በጥቅም የለወጡ ዲያስፓራዎች ዓለም ባንክንና የዓለም የገንዘብ ድርጅትን (IMF) ተክተው ህወሓት ስላስገኘው ፈጣን እድገት በአገዛዙ ራድዮ እና ቴሌቪዥን ሲነግሩን መስማት ያሳፍራል። የህወሓት አገዛዝ “ፍትህን፣ መልካም አስተዳርንና ዲሞክራሲን አስፍኗል፤ ይህንንም መጥተን በዓይኖቻችን ተመልክተናል” እያሉ የግፉን ገፈት እየቀመስን ላለነው ሲነግሩን መስማት ያማል።
እነዚህ ወገኖቻችን ህወሓትን በማሞካሸት የሚያገኙት መሬት ብዙ ድሆች የተፈናቀለቡት፤ ለእነሱ በብላሽ የተሰጠው ብድር በረሃብ ለሚጠቃ ወገን የተላከ እርዳታ መሆኑ ማሳሰብ ይገባል። ከህወሓትና አጫፋሪዎቹ ጋር ተስማምተው ባገኙት ገንዘብ የሚቆርሱት እያንዳንዱ እንጀራ የብዙ ወገኖቻችን ደምና እንባ የፈሰሰበት መሆኑ ማስገንዘብ ያሻል። ከህወሓት ጋር በማበር በወገኖቻችን ድህነትና ችጋር እየከበሩ ያሉ የዲያስፓራ ማኅበረሰብ አባላት ከዚህ እኩይ ሥራቸው እንዲታቀቡ ማስጠንቀቅ ይገባል። እኚህ ወገኖች የራሳቸው ክብር ማጉዳፋቸውን ብቻ ሳይሆን የልጅ ልጆቻቸውም የሚያፍሩባቸው መሆኑን ማስታወስ ይገባል። ከዚህም አልፎ የዛሬ ተግባራቸው ነገ በህግ የሚያስጠይቃቸው መሆኑን ሊያውቁ ይገባል።
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ለግል ጥቅማቸው ሲሉ የአገዛዙን እድሜ በማራዘም ላይ የተሰማሩ፤ በድሆች ድህነት ለመክበር በመሯሯጥ ላይ ያሉ፤ ለግል ጥቅማቸው ሲሉ ለአገዛዙ ጥብቅና የቆሙ የዲያስፓራ አባላት ከዚህ ተግባራቸው እንዲታቀቡ ያሳስባል።
አርበኞች ግንቦት 7 “ከህወሓት ውድቀት በኋላ ያለው ጊዜ ለእናንተም ከዛሬው የተሻለ ይሆናል። ዛሬ ከህወሓት ጋር ያላችሁን ሽርክና አቋርጡ። ለነፃነት የሚደረገውን ትግል እርዱ፤ መርዳት ባትችሉ እንቅፋት አትሁኑ፤ አለበለዚያ ግን ከተጠያቂነት የማታመልጡ መሆኑን እወቁ” ይላል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!! !

onsdag 26. august 2015

ከ50 የማያንሱ የመኢአድ የአመራር አባላት በወያኔ ታሥረዋል

aeup-logo-


ቁጥር 001
ቀን 29/10/2007 ዓ.ም
ለሚመለከተው ሁሉ
ጉዳዩ፡- በእስር ላይ ስላሉ አመራና አባላትን ይመለከታል፡፡
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጥቅምት 28-30/2007 ዓ.ም በጠቅላላ ጉባኤ የተመረጠው አመራር በምርጫ ቦርድ እውቅና ተነፍጎት ለሁለተኛ ጊዜ ጥር 3/2007 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በምርጫ ቦርድ አስገዳጅነት ሁለት ጊዜ ጉባኤ አካሂዷል፡፡ ሁለተኛውም ተቀባይነትን ተነፍጎ ፕሬዝደንቱን አቶ ማሙሸት አማረን ጨምሮ በፖሊስ ኃይል አመራርና አባላቱ ከመኢአድ ጽ/ቤት በግፍ እንዲወጣ ተደርጓል በምትኩ ጠቅላላ ጉባኤ ያልመረጠው የሥርዓቱ አገልጋይ የሆነው አቶ አበባው መሐሪ ለተባለ ግለሰብ ጽ/ቤቱን በምርጫ ቦርድ ፖለቲካዊ ውሳኔ ተረክቧል፡፡
ይህ ከጽ/ቤቱ በፖለቲካዊ ውሳኔ እንዲወጣ የተረገው አመራር እና አባላት በመላ ሀገሪቱ በልዩ ልዩ እስር ቤቶች ታስረው ይገኛሉ፡፡ የአብዛኞቹም አመራርና አባላት ያሉበት ሁኔታ እጅግ አሳስቦናል፡፡
ስለዚህ በስም የጠቀስናቸው 37 (ሰላሳ ሰባት) አመራርና አባላት እንዲሁም በስም ያላወቅናቸው የእነ መቶ አለቃ ጌታቸው መኮንን የክስ መዝገብ ሥር የተከሰሱ ሰዎች በእነ ዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ሥር 5 (አምስት) ሰዎች ስላሉበት ሁኔታ በእናንተ በኩል አስፈላጊውን ክትትል ታደርጉ ዘንድ እናሳስባለን፡፡
ከሠላምታ ጋር
በእስር ላይ የሚገኙ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)
አመራር አባላት ስም ዝርዝር
ተ.ቁ ስም ዝርዝር የመኖሪያ አድራሻ አካባቢ ክ/ሀገር በፓርቲ ውስጥ የነበረው ኃላፊነት ታስረው ያሉበት እስር ቤት የታሰሩበት ጊዜ
1 ማሙሸት አማረ አዲስ አበባ ሊቀ መንበር ቅሊንጦ ግንቦት 5/2007 ዓ.ም
2 ዘመነ ምህረት ሰ/ጎንደር/ማክሰኝት/ ም/ሊቀ መንበር ቅሊንጦ ጥር 10/2007 ዓ.ም
3 አብርሃም ጌጡ አዲስ አበባ የውጪ ግንኙነት አ.አ ፖሊስ ኮሚሽን 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ ሰኔ 12/2007 ዓ.ም
4 ኢያሱ ሁሴን አላማጣ ማህበራዊ ዘርፍ አላማጣ ህዳር/2007 ዓ.ም
5 ዘመነ ጌጤ አዲስ አበባ የወታት ማህበራዊ ዘርፍ ቅሊንጦ ሚያዚያ/2007 ዓ.ም
6 በላይ ዳኘው አላማጣ አባል /አላማጣ/ ቅሊንጦ
7 ሞላ መለሰ አላማጣ አባል /አላማጣ ቅሊንጦ
8 ጥጋቡ ሙላት አላማጣ አባል /አላማጣ/
9 ጥላሁን አድማሴ ጎንደር አባል /ጎንደር/
10 ጌትነት ደርሶ ጎንደር አባል /ጎንደር/ ቅሊንጦ
11 ጥላሁን አበበ ጎንደር አባል /ጎንደር/
12 መለሰ ሰጠኝ ጎንደር አባል /ጎንደር/ ቃሊቲ
13 አስራት እሸቴ ሰሜን ሸዋ አባል /ሰሜን ሸዋ/ ቅሊንጦ መስከረም/2007 ዓ.ም
14 ተስፋዬ ታሪኩ ጎጃም አመራር /ጎጃም/ ቅሊንጦ መስከረም/2007 ዓ.ም
15 ፻አለቃ ጌታቸው መኮንን ጎጃም አመራር /ጎጃም/ ቅሊንጦ
16 ኢንጂነር መለሰ ሰጤ ጎጃም አባል /ጎጃም/ ቃሊቲ ግንቦት/2003 ዓ.ም
17 አናጋው ተገኘ ጎጃም አባል /ጎጃም/
18 አባይ ዘውዱ ጎጃም አባል /ጎጃም/
19 እንግዳው ዋኘው ጎጃም አባል /ጎጃም/
20 በላይነህ ሲሳይ ጎጃም አባል /ጎጃም/
21 አለባቸው ማሞ ጎጃም አባል /ጎጃም/
22 ታጀበ አለኸኝ ጎጃም አባል /ጎጃም/
23 ዮሐንስ ገደቡ ጎጃም አባል /ጎጃም/
24 አዝመራው ከፍአለ ጎጃም አባል /ጎጃም/
25 ተስፋዬ አስማረ ጎጃም አባል /ጎጃም/
26 ችሎት ጎበዜ ጎጃም አባል /ጎጃም/
27 መለሰ መንገሻ አዲስ አበባ የወጣት ድርጅት ጉዳይ ቅሊንጦ ጥር/2007 ዓ.ም
28 ሞገስ አሰፋ ደሴ አባል ደሴ ሰኔ/2007 ዓ.ም
29 ዘሪሁን በሬ አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
30 አወቀ ሞኝሆዴ አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
31 አማረ መስፍን አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
32 አትርሳው አስቻለው አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
33 አግባው ሰጠኝ አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
34 ወርቅየ ምስጋና አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
35 ቢሆነኝ አለነ አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
36 ታፈረ ፋንታሁን አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
37 ፈረጀ ሙሉ አባል ቅሊንጦ ያልታወቀ
38 አሸናፊ አካሉ ጎንደር አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
39 ደህናሁን መአዛ ጎንደር አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
40 ምንዳዬ ጥላሁን ጎንደር አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
41 አንሙት የኔዋስ ጎንደር አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
42 መንግስቱ አስቻለ ጎጃም አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
43 በላቸው አወቀ ጎጃም አባል ቅሊንጦ 2005 ዓ.ም
44 መምህር ስማቸው ምንይችል ጎጃም አባል ያልታወቀ 2007 ዓ.ም
45 አበባዉ አያለዉ ም/ጎጃም አባል ባሕር ዳር
46 ብርሀኑ ካሳሁን ም/ጎጃም አባል ያልታወቀ ያልታወቀ
47 ብችል ቀሪ ባሕር ዳር አባል ያልታወቀ ያልታወቀ
48 ቴዎድሮስ አያለዉ ሰ/ወሎ አባል ዝዋይ ያልታወቀ
49 እዳልካቸዉ መለሰ ሰ/ወሎ አባል ዝዋይ ያልታወቀ
50 ማንደፍሮ አካልነዉ ላሊበላ አባል ዝዋይ ያልታወቀ
ለገሰ ወ/ሐና
የመኢአድ ም/ሕዝብ ግንኙነት ሐላፊ

[ሙሉውን መግለጫ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ]—

- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9898#sthash.pakcqJD3.dpuf

mandag 24. august 2015

የወያኔ የመከላከያ ሰራዊት አባላት “የተቃዋሚዎች ሬድዮ ታዳምጣላቹ በሚል እየታሰሩ ነው

11899854_458103757685979_3718763112024142931_n
በገዢው ስራዓት የመከላከያ ሰራዊት ውስጥ እየተካሄደ ባለው ሰፊ የዓመቱ ግምገማ “የተቃዋሚዎች ሬድዮ መስማት” እንደዋነኛ መገምገሚያ ነጥብ ሆኖ መነሳቱን ተገለፀ።በምንጮቻችን መረጃ መሰረት- በሁሉም የስርዓቱ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ እየተካሄደ ያለውን መጠነ ሰፊ የዓመቱ ግምገማ ወታደሩ ያለማቋረጥ እየፈረሰ በመጥፋት ላይ ያለው የትጥቅ ትግል እያካሄዱ በሚገኙ ድርጅቶች የሚሰራጨውን ሬድዮ መስማት ዋናው ከሆኑ ምክንያቶች አንዱ ስለሆነ ለምን ታዳምጣላችሁ፤ እነማን ናቸው የሚያዳምጡት መታወቅ አለባቸው በማለት እየተካሄደ ባለው ስብሰባ የሰራዊቱ አዛዦች ራሳቸው የስብሰባው መሪዎችና ገምጋሚዎች ሆነው በመቅረብ ለበርካታ የሰራዊቱ አባላት እያባረሩና እያሰሩ መሆናቸው ተገልጿል።
በተለይ በሰሜን እዝ እየተካሄደ ባለው የዓመቱ ግምገማ ላይ የሰራዊቱ አባላት ሓቀኛና ገምቢ ግምገማ ነው ብለው ስላላመኑበት ማንኛውም ሃሳብ ከመስጠት እንደተቆጠቡና የስርዓቱ ተጠቃሚዎች የሆኑት የበላይ መኮነኖች “እዚህ የተሰበሰብነው ሰራዊቱ አንዣቦበት ካለው የመበታተን አደጋ ለማዳን ስለሆነ የተቃዋሚዎች ሬድዮ ለምን ትሰማላችሁ ብለው ላቀረቡት ሃሳብ በተሰብሳቢዎቹ ማንኛውም ሚድያ መከታተል የዜጎች ህገ መንግስታዊ መብት ነው” ብለው የተቃወሙትን የናንተ አመለካከት ከተቃዋሚዎች ጎራ ነው በማለት እንድፋሰርዋቸው መረጃው ጨምሮ አስርድቷል።
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9822#sthash.qvLwE9KZ.dpuf

fredag 21. august 2015

ወጣቶቹን እየበላ ያለው ስርዓት … (ግርማ ሠይፉ ማሩ)

ግርማ ሠይፉ ማሩ
  • 116
     
    Share
ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ በቀጣይ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ የተመረጡ እና የተለመዱ ፊቶችን ስብስበው ጥያቄ ሲያቀርቡና ማብራሪያ ሲሰጡ ነበር፡፡ የእኔን ቀልብ የሳበው ግን አውቀውም ይሁን ሳያውቁት ወጣቶችን እየበላ ያለ ስርዓት ባለቤት እና መሪ መሆናቸውን የገለፁበት አስተያየት ከታዳሚው ሞቅ ባለ በተደጋጋሚ ጭብጨባ መታጀቡ ነው፡፡ ባለፈው የኦባማ ጉብኝት ወቅት ዲሞክራሲ ማላት ምርጫ በስላም ማጠናቃቅ ብቻ አይደለም፡፡ ጋዜጠኞችን አክቲቪሰቶችን እስር ቤት እያወረዱ አማራጭ ፖለቲካን እየከለከሉ ዲሞክራሲ የተሟላ አይሆኑም ብለው ሲሞልጯቸው በጭብጨባ ያጅቡ ነበር፡፡ ዛሬም ተመሳሳይ ነገር ነው የሆነብኝ፡፡
ይህን ፅሁፍ ከመለጠፌ በፊት ግን በእስር ላይ ያሉ ጓዶቻችን ከእስር እንዲፈቱ ፍርድ ቤት መበየኑን ሰምቻለሁ፡፡ ንፁህ ናችሁ ብሎዋቸዋል፡፡ ንፁህ ነበሩ እና አይገርምም፡፡ ይህን ማበረታታት አለብን፡፡ እነ አንዱዓለም፣ ናትናኤል፣ እስክንድር፣ ተመስገን ደሳለኝ ፣ ወዘተ መለቀቅ አለባቸው፡፡ ይህን ጥሩ እርምጃ ኦባማ ተቆጥቷቸው ነው እያሉ ከማንቋሸሽ ይህን እያጣጣምን ተጨማሪ መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ለማነኛውም ለቤተሰቦች ዕዳ ሆነው የነበሩት ታጋዮች ነፃ ወጥተዋል፡፡ ከቂሊንጦ!!! እንኳን ደስ ያላችሁ ደስ ያለን!!!
ወደ ተነሳሁብ ነጥብ ሰመለስ ጠቅላይ ሚንስትሩ ጉቦ የሚበላባቸው መስሪያ ቤቶች እንዳሉ ማወቅ ብቻ አይደለም ወጣቶችንም ጉበኛ አድርጎ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አስልጥኖ ወደ ተግባር እንደሚያስገባ በግልፅ ነግረውናል፡፡ በተጨማሪ ምንም ዓይነት የተሟላ ማስረጃ ቢኖረን ጉዳያችንን መጨረስ የማንችልባቸው የመንግስት ተቋማት እንዳሉም ጠቅላይ ሚኒስትራችን ጠንቅቀው ያውቃሉ እነዚህም ተቋሞች የሰለጠኑ አዲስ ምሩቃን ወጣቶች ስራ እንዲሰሩ ሲመደቡላቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዴት ጉዳይ ማለቅ እንደሌለበት ጠንቅቀው ይማራሉ፡፡ ይህንንም በተግባር ይፈፅሙታል፡፡ እነዚህ መስሪያ ቤቶች የመንግስት አገልግሎት መስጫ ነው፡፡
ባለጉዳይን በአግባቡ እና በስርዓት ያለማስተናገድ በእርሰቸው ቃል አመናጫቂና አንጓጣጭ መስሪያ ቤቶችም እንዲሁ የተመደቡላቸውን ወጣት ምሩቃን በፍጥነት ቀይረው ተገዶ አገልግሎት ፍለጋ የመጣውን ተገልጋይ ያመናጭቃሉ፣ ይሳደባሉ፡፡ ይህን ስስማ የጤና ባለሞያዎቻችን ወላዶችን በምጥ ወቅት ማን አርግዥ አለሽ አትጩሂ ሲሉ ተሰማኝ፡፡ ሌሎች የሚሉትን ፀያፍ ቃል ለዚህ ፅሁፍ ስለማይመጥን ዘልየው ነው፡፡
የሀገር ውስጥ ገቢ ኦዲተሮች እና ገማቾች በግብር ከፋይ ዜጎች ላይ ያላቸውን “ቬቶ ፓውር” ማወቅ ብቻ አይደለም፣ ጠቅላይ ሚኒስትረ ተሰፋ የቆረጡበት ሁኔታ ያለ የሚመስል አስተያየት ነው የሰጡት፡፡ ሂሳብ ሰርታችሁ ካልመጣችሁ እንደፈለጉ ያድርጓችሁ የሚሉን ይመስላል፡፡ ለአፋቸው እንኳን እነዚህን ልክ ማስገባት አለብን የሚል ተሰፋ አልሰጡንም፡፡ እኔ በግሌ የሀገር ውስጥ ኦዲተር ብሆን ስራ አቆም ነበር፡፡ ደግነቱ እግዜር አንድኖኛል፡፡ በእኛ ሀገር መስሪያ ቤቱ ሲሰደብበት ኃላፊነቱን የሚለቅ ባለስልጣን ስለሌለን ነው፡፡ እራሴ እለቅ ነበር ያልኩት፡፡
እነዚህን ሁሉ ወጣቶችን የሚበሉ መስሪያ ቤቶች የሚተዳደሩት በመንግሰት በጀት፣ በምርጫ አሸንፌ ስልጣን ያዝኩ በሚል መንግሰት በሚሾሙ የፖለቲካ ሾመኞች መሆኑን የዘነጉት ይመስላሉ፡፡ ይህን ለማለት ያስቻለኝ ደግሞ መፍትሄው የታጋይ ዜጋ መኖርና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ነው በማለት አስቀምጠው፣ የፖለቲካ ቁርጠኝነት በተመለከት ጠንካራ ፓርቲና አመራር በመኖሩ ተገባራዊ ማድረግ ይቻላል በሚል አሹፈውብናል፡፡
ይህን ፕሮግራመ የተከታተልን ሰዎች ታጋይ ዜጎችን በእኔ ትርጉም እንቢ ሙሰኝነት ….. ያሉትን፣ የመልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የጮሁትን እና የዘመሩትን፣ መንግሰት ይህን ጉዳይ የማያውቅ ከሆነም እንዲገባው የጦመሩትን፣ የፖለቲካ ሙሰኝነት እንዲቀር እንቅልፉን አጥቶ ጋዜጣና መፅሄት በማዘጋጀት የሚተጉትን ጋዜጠኞችን እስር ቤት እያጎሩ እንዴት ታጋይ ዜጋ እንደሚፈራ አልታይህ አለኝ፡፡
ታጋይ ዜጋ እንዳይፈራ ዜጎችን አንገት እያስደፉ ፖለቲከኞች በሚፈነጩበት ሀገር ኪራይ ስብሳቢነት አንገቱን እንዴት እንደሚደፋ ማወቅ አይቻልም፡፡ ታጋዮችን አንገት አስደፍቶ ሌቦች ፖለቲከኞችን ቁርጠኞች ናቸው ማለት ፌዝ ነው፡፡
ታጋይ ዜጋ እናፍራ – ታጋይ የሆነ ዜጋ ጉቦ አይከፍልም በዚህ ጊዜ ኪራይ ስብሳቢነት ይደፈቃል ነው ብለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነገር ግን ጉቦ አልሰጥም የሚል ዜጋ ለማፍራት፣ ከፖለቲከና ዱላ የሚጠብቅ ሲቪል ማህበረሰብ፣ ጋዜጠኛ የግድ ይለናል፡፡ ፍርድ ቤት ያስፈልገናል፡፡ ያስቸገሩንን ወሰደን የምንገትርበት፡፡ የመርጊያ በቃናን ውሳኔ የሚያፀና ፍርድ ቤት አለን ብለን ጉቦ አንከፍልም በሉ ብለን እዝቡን ለጅብ አንሰጥም፡፡ መልዕክቴ ስርዓቱ ከፖለቲካ ሙሰና ከፀዳ እርገጠኛ ይሁኑ ሌሎች ሙስናዎች ተራ ናቸው፡፡ ለማነኛውም ይህ ወጣቶችን እየበላ ያለው የፖለቲካ ስርዓት ይገራልን፡፡
ቸር ወሬ ያሰማን!!!!! ዛሬ ደስ ብሎኛል ደስ ይበላችሁ!!!!
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9727#sthash.PyNQLVuH.dpuf