torsdag 26. februar 2015

ምርጫ ለኢትዮጵያ ወታደርና ፓሊስ: – ለህወሓት ባርነት ወይስ ለኢትዮጵያ ነፃነት

February 26,2015
pg7-logoየኢትዮጵያ ሕዝብ ለውትድርና ከፍተኛ ክብር አለው። ውትድርና ከሙያና ሥራ በላይ የነፃነትና የክብር መገለጫ፤ ሀገርን ከባዕድ ወረራ መከላከያ ጋሻ ነው ብሎ ያምናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ህግና ሥርዓት አክባሪ በመሆኑ ለፓሊስም ከፍተኛ አክብሮት አለው። የፓሊስ ሥራ ወንጀልን መከላከልና ወንጀለኞችን ወደ ፍርድ ማቅረብ መሆኑ በኢትዮጵያ ባህል የተከበረ ቦታና እውቅና አለው።
በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ግን ይህ እየተቀየረ ነው። የህወሓት አዛዦች እየመሩት ያለው የኢትዮጵያ ጦር ሠራዊት ሀገርን ከባዕድ ጠላት ከመከላከል ጋር ምንም ዝምድና በሌላቸው ሁለት አበይት ተግባራት ላይ ተጠምዷል። በህወሓት አዛዦች የሚመራው ሠራዊት ዋነኛ ተግባር ለሰብዓዊ መብቶቻቸው መከበር እና ለፍትህ መስፈን የሚታገሉ ዜጎችን ማጥቃት ሆኗል። የጦሩ ሁለተኛው አቢይ ተግባር ደግሞ ለአዛዦች የግል ጥቅም ማካበቻ ገቢዎችን በሚያስገኙ ሥራ ላይ መሠማራት ነው።
የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት ኢትዮጵያዊያንን ማጥቂያ ሠራዊት መሆኑ ሲቪሉን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የሠራዊቱንም አባላትን ጭምር ለህሊና ወቀሳ የዳረገ ጉዳይ ነው። ሆኖም ግን ይህ በህሊና ወቀሳ ብቻ ሊታለፍ የማይችል ወንጀል ነው። ሠራዊቱ በህወሓት እየታዘዘ የሚዘምተው በገዛ ራሱ ልጆች፣ እህቶች፣ ወንድሞችና ወላጆች፤ በገዛ ራሱ ጥቅሞች እና በገዛ ራሱ ላይ መሆኑ መገንዘብ ይኖርበታል። በገዛ ራሱ ጥቅሞች ላይ የሚዘምት አንድም ህሊና የሌለው አሊያም ነፃነት የተነፈገው ሰው ብቻ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ሠራዊቱ እየተራበና እየታረዘ አለቆቹ የታላላቅ ህንፃዎች ባለቤቶች፣ ባለፋብሪካዎች፣ የባንክና የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ባለአክሲኖች የሚሆኑበት ሥርዓት ከዳር ሆኖ የሚመለከት መሆኑ የሚገርም ነው። ሠራዊቱ ቤተሰቦቹን መመገብ አቅቶት እያለ የአዛዦቹ ልጆች ለሽርሽር ዓለምን ይዞራሉ። እንዴት ነው ሠራዊቱ እየደኸየና እየሞተ አዛዦቹ እየከበሩ የሚሄዱት? ይህ አዋራጅ ሁኔታ እንዲያበቃ መታገል የሠራዊቱ ግንባር ቀደም ኃላፊነት ነው። ሠራዊቱ ወይ ባርነትን አሜን ብሎ መቀበል አለበት አለበዚያም እሱም እንደነሱ ሰው መሆኑን ማሳየት መቻል አለበት። በኢትዮጵያ ውስጥ የህወሓት አገዛዝ ወድቆ የሕዝብ ይሁንታ ያገኘ መንግሥት መመሥረቱ በከፍተኛ ሁኔታ ከሚጠቅማቸው የኅብረተብ ክፍሎች ግንባር ቀደሙ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ናቸው። በዚህም ምክንያት የሠራዊቱ አባላት ለሥርዓቱ መውደቅ በግልጽም በስውርም መታገል የዜግነት ብቻ ሳይሆን አዕምሮ ያለው ሰው ሆነው በመፈጠራቸው የተቀበሉት ግዴታ ነው።
ፓሊስን በተመለከተም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ህወሓት የኢትዮጵያን ሕዝብ አፍኖ ለመግዛት የቻለው በዋኛነት የፓሊስን ኃይል ለአፈናው ተግባር የሚጠቀም በመሆኑ ነው። የተቃውሞ ድምጾች በተሰሙ ቁጥር የኢትዮጵያ ፓሊስ በወገኖቹ ላይ የሚያወርደው ዱላ የሚዘገንን ሆኗል። ሰላማዊ ሰልፈኞችን በጥይት መግደልና ማቁሰል፤ አረጋዊያንን፣ ሴቶችንና ሕፃናትን መግደል፣ ማቁሰል፣ መደብደብ በዚህ ተግባር የተሠማሩ ፓሊሶችን በቡድንም በግልም በህግ የሚያስጠይቅ ከባድ ወንጀል ነው። በህወሃት እየተመራ ያለው የኢትዮጵያ ፓሊስ ተግባራት ተበዳዮችን ብቻ ሳይሆን ራሱ ፓሊስንም ጭምር አንገት የሚያስደፋ ተግባር ነው። ለመሆኑ አንድ ተራ የኢትዮጵያ ፓሊስ ባልደረባ ከህወሓት አገዛዝ ምን ተጠቀመ? መልሱ “ምንም” የሚል ነው። ይልቁንስ በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ፓሊስ የተናቀና የተዋረደ ሥራ ሆነ። በህወሓት አገዛዝ ፓሊስ እንደሰለጠነ አዳኝ ውሻ “ያዝ” ሲሉት የሚነክስ፣ የሚያደማ፣ የሚቦጭቅ ሆኗል። ይህ ለፓሊስ፣ ወንጀልም ውርደትም ነው። በህወሓት አገዛዝ መገርሰስ እና በምትኩ የህግ የበላይነት የሰፈነበት ሥርዓት መስፈን ፓሊስ ከሁሉ በላይ ተጠቃሚ ነው፤ ሰብዓዊ ክብሩን ያረጋግጥለታልና።
ዛሬ በኢትዮጵያችን ውስጥ የታዘዙትን የሚፈጽሙ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት አባላት ስላሉ ነው የህወሓት ሹማምንት ልባቸው ያበጠው። ለማስረጃ ያህል ሰሞኑን የህወሓቱ ሹም አባይ ፀሐዬ የአዲስ አበባ ዙሪያ ገበሬዎች በግዴታ መነሳታቸው የሚቃወሙትን ዜጎችን ሁሉ ”ልክ እናስገባቸዋለን” ብሎ በሸንጎ የዛተው የታዘዘውን የሚፈጽም የጦርና የፓሊስ ሠራዊት መኖሩን ተማምኖ ነው። እስከ መቼ የኢትዮጵያ ጦር ሠራዊትና ፓሊስ ሕዝብን ማስፈራሪያ መሣሪያ ይሆናል?
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የኢትዮጵያ የመከላከያና የፓሊስ ሠራዊት አባላት ለራሳቸው እና ለወገናቸው የሚበጀው ሥርዓት የቱ እንደሆነ ያውቃሉ ብሎ ያምናል። በዚህም ምክንያት ስብዕናቸውን እያዋረደ እና እያደኸያቸው ያለውን የህወሓት አገዛዝን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በመሆን ይፋለሙታል ብሎ ያምናል። ይህ ውሳኔ ግን ሠራዊቱ በጅምላ ሳይሆን እያንዳንዱ የሠራዊቱ አባል በግሉ የሚወስደው ውሳኔ እንደሆነ አርበኞች ግንቦት 7 ይገነዘባል።
በዚህም መሠረት ተደጋጋሚ ጥሪ እየተደረገለት፤ ጥሪውንም እየሰማ ከህወሓት ጋር ወግኖ ሕዝብን መውጋት የቀጠለ የሠራዊቱ አባል ላደረሰው ጥፋት በግል መጠየቁ የማይቀር መሆኑ ሊገነዘብ ይገባል። በእያንዳንዳንዱ የጦርና ፓሊስ ሠራዊት ባልደረባ ፊት የቀረበው ምርጫ “ለህወሓት ባርነት ታድራለህ ወይስ ራስህንና ሀገርን ነፃ ታወጣለህ” የሚል ነው።
ራስህንና ሀገርህን ነፃ ለማውጣት የመረጥክ የሠራዊቱና የፓሊስ ባልደረባ አሁኑኑ ሕዝባዊ ትግሉን ተቀላቀል። እስከዛሬ የበደልከውን ሕዝብ ለመካስ ምቹ ሁኔታ አለህ። በግልጽ የነፃነት ኃይሎችን እንድትቀላቀል፤ አሊያም አለህበት ሆነህ በውስጥ አርበኝነት እንድትደራጅና ተግባራዊ ሥራ እንድትጀምር መንገዱ ተመቻችቶልሃል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

torsdag 19. februar 2015

የ2007ቱን ሀገራዊ ምርጫ ሂደት እና ከምርጫዉ ዉጭ ያሉ አዋጭ አማራጮችን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የአቋም መግለጫ

አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሰላማዊ፣ ተዓማኒና ፍትሀዊ በሆነ ምርጫ የማይፈልጋቸውን መሪዎች መሻር፤ የሚፈልጋቸውን ደግሞ መሾም የሚያስችሉትን መሠረቶች ለመጣል የሚታገል ንቅናቄ ነው። እንደሚታወቀው የሕዝብ እውነተኛ ፍላጎት የሚገለጽበት እውነተኛ ምርጫ እንዲኖር ገለልተኛና ቀልጣፋ የፍትህ ሥርዓት፣ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት ሊኖሩ ይገባል። ነፃ የሚዲያ ተቋማትና በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማኅበራት መኖርም መታለፍ የሌለባቸው አቢይ ጉዳዮች ናቸው። አማራጭ ፓሊሲዎችን ማቅረብ የሚችሉ በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የፓለቲካ ፓርቲዎች ከሌሉም አማራጮች የሉምና ምርጫ ትርጉም የለውም። ይህ ሁሉ ቢሟላ እንኳን ምርጫውን የሚያስፈጽመው አካል ገለልተኛ፣ ሀቀኛና ተዓማኒ ካልሆነ የሚደረገው ምርጫ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት የሚያንፀባርቅ ሊሆን አይችልም።
g 7ከላይ የተዘረዘሩትን የምርጫ እሴቶች ሙሉ በሙሉ ባይሆንም እንኳን የተወሰኑትን በመጠኑም ቢሆን ያካተተ ምርጫ እንዲኖር መጣርና በሂደት የምርጫውን አፈፃፀም ማሻሻል ይቻል ይሆናል በሚል እምነት የዲሞክራሲ ኃይሎች በህወሓት የሴራ ምርጫዎች ሲሳተፉ ቆይተዋል። ሆኖም በህወሓትና በእውነተኛ ምርጫ መካከል  ያለው ተቃርኖ እያደር እየሰፋ ሲሄድ እንጂ ሲጠብ አልታየም።  በህወሓት ሙሉ ቁጥጥር ስር በሚካሄድ ምርጫ ኢትዮጵያን የሚጠቅም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚለው እምነት ለአርበኞች ግንቦት 7 ፈጽሞ የተሟጠጠው ከምርጫ 97 ማግስት ጀምሮ  ነው። በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓም የኢትዮጵያ ሕዝብ በታላቅ የለውጥ ተስፋ የሰጠው ድምጽ በህወሓት የተዘረፈው ከላይ የተዘረዘሩት ተቋማት ያልነበሩ በመሆናቸው፤ ስለዚህም ከምርጫ በፊት ተቋማቱን መገንባት፤ ተቋማቱን ለመገንባት ደግሞ ህወሓትን ከስልጣን ማስወገድ ይገባል ብሎ በማመኑ ነው አርበኞች ግንቦት 7 በሁለገብ የትግል ስልት በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው።
ያም ሆኖ ግን በምርጫ ላይ ያላቸው ተስፋ ፈጽሞ ያልተሟጠጠ ፓርቲዎችን በማክበርና ሥራቸውንም አስቸጋሪ ላለማድረግ ሲባል ከምርጫ 97 ወዲህ የነበሩ ብሄራዊም ሆነ ክልላዊ ምርጫዎችን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምርጫ ዉጭ ያሉ ሌሎች አማራጮችን ብቻ እንዲመለከት አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ አድርጎ አያውቅም ነበር። አሁን ግን የአገራችን ኢትዮጵያ የፓለቲካ ሁኔታዎች  ይህንን የቆየ አቋም በሚያስቀይር መንገድ፤ የአገራችንን የወደፊት ዕድል ብቻ ሳይሆን ባጠቃላይ ያካባቢውን ሰላም በሚጎዳ መልኩ ተቀይሯል። የሰሞኑ የወያኔ እርምጃዎች ትንሽ ተስፋ ያደርግ የነበረውን የዴሞክራሲ ወገንተኛ ተስፋም እምሽክ አድርጎ በልቶታል:: እየተቃረበ ያለው ዓይነት የፌዝ ምርጫ ወያኔ እንደ እንጄራ የራበውን የተቀባይነት እጦት ለአጭር ጊዜ ያስታግስለት ይሆናል እንጂ የሀገሪቱን እያደር እየተወሳሰበ የመጣ ችግር ለጊዜውም እንኳን የሚያስታግስ አይሆንም፤ ይልቁንም ጊዜው በገፋ ቁጥር ችግሩ መቋጠሪያ የጠፋው እየሆነ ይሄዳል::
የሁኔታውን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር የወቅቱን የአገራችን የፓለቲካ ሁኔታ በጥንቃቄ መርምሮ የሚከተሉት ግንዛቤዎች ላይ ደርሷል።
  1. ህወሓት ብዙዎች እትዮጵያዊያን የተሰውላቸውን አንድነት ፓርቲንና መኢአድን በመበተን የድርጅቶቹን ስምና ንብረት ለአገልጋዮቹ መስጠቱ፤ ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው የመራጭን ድምጽ መስረቅ ሳይበቃው የምርጫ ተወዳዳሪንም መዝረፍ መጀመሩን አመላካች ነው። ይህ ተግባር ህወሓት የምርጫ ውጤትን ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችንም እሱ ራሱ ለመምረጥ መወሰኑን ያሳያል፤ ከዚህ በተጨማሪ የሴራ ምርጫውን ከጅምሩ ጀምሮ አስቀድሞ እስከተወሰነለት መዳረሻው ድረስ ለምንም ዓይነት ያልተጠበቀ አጋጣሚ (በምርጫው ወቅት የሚደረጉትን ክርክር ተብዬዎች ጨምሮ) እድል ላለመስጠት ወስኖ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በግልጽ ያሳያል፤
  2. ይህ እኩይ ውሳኔ በምርጫ ቦርድ ፊርማና አንደበት ቢነገርም ምንጩ የህወሓት ፓሊት ቢሮ  መሆኑን የሚከተሉት ተግባራት ይጠቁማሉ፤
2.1.         በምርጫ ቦርድ በኩል እንዲገለጽ የተወሰነው እርምጃ ለማስመሰል ያክልም ቢሆን የህጋዊነት ሽፋን እንዲኖረው አለመደረጉ ውሳኔው ፍጹም እብሪተኛ በሆነ አካል መወሰኑን ያመለክታል። እንዲህ                   ዓይነቱ እብሪተኛ አካል ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ነው። ውሳኔውን ለማስፈፀም የነበረው ጥድፊያም ይህንኑ ያጠናክራል።
2.2.        ለማስመሰያ ያክል እንኳን ምንም አይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሳይኖር ፓሊስ የአንድነትና የመኢአድ ቢሮዎችን መውረሩ፤ ህወሓት አንድነትንና መኢአድን አጥፍቶ የድርጅቶቹን ስሞችና ንብረቶች                   ለሚፈልጋቸው ሰዎች ሰጥቶ በአስቸኳይ ለምርጫ ድራማው በፊት መስመር ሊያሰልፋቸው መወሰኑን አመላካች ነው። እንዲህ ዓይነት ከባድ ውሳኔ የሚሰጠው ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ብቻ                    ነው።
2.3.        ወደ ፈቃድ መንጠቅ ከመደረሱ በፊትም በሰማያዊ ፓርቲ፣ በአንድነትና በመኢአድ አባላት የደረሰው አረመኔያዊ ድብደባ፤ ንቁ የፓለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉ ዜጎች ላይ የሚደርሰው እስር፣ መሰወርና                 እና ባልታወቁ ሰዎች ተገድሎ መገኘት መብዛት እነዚህን አገራዊ ፓርቲዎች የመበተን የፓለቲካ ውሳኔ መሰጠቱን አመላካቾች ናቸው።
  1. ለጊዜው የፈቃድ ነጠቃና የንብረት ዘረፋ የተፈፀመው በአንድነትና በመኢአድ ላይ ቢሆንም በሰማያዊ ፓርቲ ላይ በየእለቱ እየጠነከረ የመጣው የአፈና እርምጃም በተመሳሳይ ፓርቲውን ወደማገድ አለዚያም ፈጽሞ መንቀሳቀስ ወደማይችልበት ደረጃ ሊያደርሰው ይችላል የሚል እምነት አሳድሯል። ሌሎች ፓርቲዎችም ከዚህ ህወሓት ካሰመረው የውሸት ጫወታ መስመር የመውጣት ዝንባሌ ቢያሳዩ ተመሳሳይ እርምጃ አይቀርላቸውም።
  2. የህወሓት የወቅቱ የጥፋት ዒላማ ያነጣጠረው አንፃራዊ በሆነ መንገድ የተሻለ መዋቅርና ማኅበራዊ መሠረት ባላቸው እና በአገራዊ አጀንዳዎቻቸው በሚታወቁ ፓርቲዎች ላይ መሆኑ፤ የወቅቱ የጥፋት ዘመቻ የኢትዮጵያ አንድነትን የማዳከምና ከፋፍሎ የመግዛት የህወሓት ትልቁ አጀንዳ አካል መሆኑን ያሳያል።
  3. እራሱን በዘር ያደራጀዉና ኢትዮጰያ ዉስጥ ያለዉ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ አደረጃጀት ከዚሁ እሱ ከተደራጀበት የዘር አደረጃጀት ዉጭ እንዲሆን በፍጹም የማይፈቅደዉ የወያኔ አገዛዝ፤ መጣፊያው ሲያጥረውና ወደ ማይቀረው ውድቀቱ ሲያመራ፤ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል እንዳለችው አህያ አገራችን ኢትዮጵያን በቀላሉ ወደማትወጣዉ የዘዉግ ግጭት ዉስጥ አስገብቶ ዘመናት ያስቆጠረዉ አንድነቷ እንዲፈረስ በትጋት እየሠራ መሆኑን ያሳያል።
  4. ከመለስ ዜናዊ ሞት ወዲህ ህወሓት ከሁሉን ጠቅላይ (totalitarian) አገዛዝ ወደ ፋሽስታዊ ቡድንነት ያሽቆለቆለ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ህወሓት ዘረኛ፣ ጠቅላይና ፈላጭ ቆራጭ ጨቌኝ በመሆኑ ፋሽስት ብለነዋል።  ሆኖም በታሪክ የሚታወቁ ፋሺስታዊ አገዛዞች ከፍተኛ ብሄራዊ ስሜት የነበራቸው ሲሆን የህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ ግን ብሔራው ስሜት አልባ መሆኑ ልዩ እና የበለጠ አደገኛ ያደርገዋል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን የህወሓት መሪዎችንና ጥቂት ሌሎች አጫፋሪዎቻቸውን የያዘ ለጊዜው አስተባባሪ መሪ የሌለው ሆኖም ግን የጦር ሠራዊትን፣ የስለላ መዋቅሩንና ፓሊስን ተቆጣጥሮ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያን እየገዛ ያለው ይህ አስኳል የለሽ ፋሽስታዊ ቡድን መሆኑ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን ተደላድሎ መሪ እንዲፈጥር ከተፈቀደለት አገራችንን የከፋ መከራ ውስጥ ሊከታት እንደሚችል ግንዛቤ ተወስዷል።

ከላይ በአጭሩ ከተራ ቁጥ 1 እስከ 6 የተዘረዘሩትን በማገናዘብ በግንቦት 2007 ሊደረግ የታቀደውን አምስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ የሴራ ምርጫን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር ውሳኔዎችን አስተላልፎ ከዚህ የሚከተሉት ጥሪዎችን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አቅርቧል።
  1. በምርጫ 2007 መሳተፍ ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ ሁኔታዎችን ከማመቻቸት ይልቅ ፋሽስታዊውን ቡድን የሚያጠናክርና የኢትዮጵያን ሕዝብ የወደፊት ዕድል የሚገድል በመሆኑ፣ ለፍትህ፣ ለነፃነት፤ ለዲሞክራሲና ለአገር አንድነት ግድ ያላቸው ወገኖች ሁሉ ከአሁኑ ከዚህ የይስሙላ ምርጫ ዉጭ ዓይኖቻቸውንና ሙሉ ጉልበታቸዉን በሌሎች የኢትዮጵያን ሕዝብ ነፃነት በሚያፋጥኑ አማራጮች ላይ እንዲያሳርፉ ጥሪ ያደርጋል። አርበኞች ግንቦት 7 የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ዓይን ያወጣ የሴራ ምርጫ ይልቅ መብቱን፤ ነፃነቱንና እኩልነቱን በሚያፋጥኑለት በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመፅ የትግል አመራጮች ላይ እንዲሳትፍ ለመላው ያገሪቱ ሕዝብ ጥሪ ያስተላልፋል።  ህወሓት ማኅበረሰባችንን ለመከፋፈልና ለማባላት የሚያደርገውን እኩይ ሴራ በጋራ እንድናከሽፈው ወገናዊ ጥሪ ያስተላልፋል፤ “አንከፋፈልም፤ ተከፋፍለንም አንጠቃም“ እንበል ይላል::
  2. ህወሓትን ማስወገድ የሚቻለው በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ በመሆኑ፤  ከሁለቱ አንዱንም አለመያዝ ሌላ ሰው ታግሎ ነፃነቴን ያቀዳጀኝ እንደማለት የሚቆጠር በመሆኑ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በአፋጣኝ ከእነዚህ ሁለት የትግል ዘርፎች ዉስጥ የተሻለ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ በሚለው የትግል ዘርፍ ውስጥ ተሳትፎ  እንዲያደርግ ጥሪ ያቀርባል።
  3. አርበኞች ግንቦት 7፣ በሁለቱም የትግል ዘርፎች ድርጅታዊ መዋቅሩን እያሰፋና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመተባበር በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ ህወሓትን ከስልጣን ለማስወገድ አቅዶ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ኢትዮጵያዊያን በስፋት እንዲቀላቀሉት፤ በኅብረት እንድንቆም እና የህወሓትን ውድቀትና የኢትዮጵያን ትንሳኤ እንድናፋጥን ጥሪ ያደርጋል::
  4. ያለንን አቅም በሙሉ ህወሓትን በማስወገድ ላይ ካዋልነው አንድ ጠንክር ያለ ሕዝባዊ አመጽ አገዛዙን ሊያፍረክርክው የሚችል በመሆኑ፤ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ከምርጫ ጋር ለተያያዙ ሥራዎች ሊውል ታስቦ የነበረው የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ገንዘብና እውቀት ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀሻነት እንዲውል ጥሪ ያደርጋል።
  5. በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንም በ2007 ምርጫ ላይ ጊዜና ንብረት ከማባከን ይልቅ በአንድ ልብ በኢትዮጵያ ውስጥ ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ ጥሪ ያደርጋል።   ከሁሉም ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች የተውጣጣ አካል የዚህን ጥሪ ተፈፃሚነት እንዲከታተል ቢደረግ ይበልጥ ውጤታማ ይሆናል ብሎ ያምናል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ
ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ

mandag 9. februar 2015

ወያኔ አንዳርጋቸው ጽጌን ለመጎብኘት ለጠየቁ የእንግሊዝ ፓርላማ አባላትን ፈቃድ ከለከለ::

February9,2015
- የወያኔ ባለስልጣናት የእንግሊዝ የፓርላማ ቡድን ልኡካን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን እንዳይጎበኙ ፈቃድ መከልከላቸውን ከሎንዶን ተሰማ::አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በወያኔ ከየመን ሰንአ አየር መንገድ ታፍነው በአዲስ አበባ የተለያዩ የማሰቃያ ቦታዎች ከፍተኛ ቶርች ሲፈጸምባቸው ቆይቶ በዚህ ሳምንት ወደ ቃሊቲ እስር ቤት እንደተዘዋወሩ ተጠቁሞ ነበር::
በጀርሚ ኮርቢን የሚመራው የእንግሊዝ የፓርላማ ቡድን ልኡካን ወደ ኢትዮጵያ በመሄድ አቶ አንዳርጋቸው የሚለቀቅበትን ጉዳይ ለመነጋገር እቅድ አድርገው የነበረ ቢሆንም በእንግሊዝ የወያኔ ኤምባሲ አምባሳደር ብርሃኑ ከበደ ከሎንዶን ከልኡኩ ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ ጉዞው እንደተሰረዘ ታውቋል::

ወደ አዲስ አበባ ሄደን አንዲን ለመጎብኘት በሚቀጥለው ሳምንት ያሰብነው ጉዞ በባለስልጣናት እውቅናና ፍቃድ ባለማግኘቱ ልንሰርዘው ተገደናል ሲሉ የልኡኩ መሪ ተናግረዋል::ሎርድ ዶላኪያ በእንግሊዝ ፓርላማ የፓርቲዎች ሕብረት የኢትዮጵያ ጉዳይ ምክትል ሊቀመንበር ከሚስተር ኮርቢን ጋር ሊያደርጉት ያሰቡት ጉዞን አስመልክቶ አለመፈቀዱን ተቃውመውት ግልጽ የሆነ ሂደት እንዲኖር የጠየቁ ሲሆን የአቶ አንዳርጋቸው ጠበቃ ክሊቭ ስታፎርድ ስሚዝ አንዳርጋቸውን እንዲጎበኙ እንዲፈቀድ አጥብቀው የጠየኡ ሲሆን በዚህ ሳምንት ጉዳዩን በፓርላማ እንደሚያነሱት ገልጸዋል::
የአቶ አንዳርጋቸው ባለቤት ወይዘሮ የምስራች ሃይለማርያም በእንግሊዝ የሚገኘውን የወያኔ ኤምባሲ እና አምባሳደር በሰብአዊ መብት ገፈፋ የሚያደርጉ አለቆቻቸው የገደል ማሚቱ ሆነው ያገለግላሉ ሲሉ ተችተዋል::በለንደን ዳውን ስትሬት የሚከበረው የአቶ አንዳርጋቸው የ60ኛ አመት የልደት በአል ለማክበር እና አቶ አንዳርጋቸው እንዲፈቱ የተሰበሰበውን ፊርማ ለጠቅላይ ሚኒስትር ካሜሮን ይሰጠሉ::ከዚሁ ጋር በተያያዘ የእንግሊዝ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ቶብሊስ ኢልውድ የአቶ አንዳርጋቸውን ጉዳይ ንዝህላል መሆናቸውና በአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ላይ አለማንሳታቸው ቃላቸውን በማጠፋቸው ተጠያቂ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ሲሆን ባለፈው ወር በእንግሊዝ ውጪ ጉዳይ ዲፕሎማቶች መካከል ከፍተኛ አተካሮ ፈጥሮ እንደነበር ይታወሳል::የእንግሊዝ ውጪ ጉዳይ ቃል አቀባይ እንዳሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣኖች የፓርላማ አባላቱን የጠበቃውን እና የአማካሪእን ጉብኝት መከልከላቸው አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን አስምረውበታል::
ሚኒሊክ ሳልሳዊ

søndag 8. februar 2015

ለወያኔ ዉንብድና መልሱ ህዝባዊ እምቢተኝነትና ህዝባዊ አመጽ ነዉ!


pg7-logoዘረኞቹ የወያኔ መሪዎ የኢትዮጵያን በትረ ስልጣን ጨብጠዉ በኖሩባቸዉ ባለፉት ሃያ አራት አመታት የአገራችን የኢትዮጵያን የፖለቲካ መድረክ ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ መልኩ እጅግ በጣም ከዘቀጠና ከረከሰ የወያኔ ድራማ ዉጭ ሌላ ምንም ነገር የማይታይበት አለባሌ መድረክ አድረገዉት ቆይተዋል አሁንም እያደረጉት ነዉ። አንድ ቋንቋ የሚናገሩትና ተመሳሳይ አመለካከት ያላቸዉ የወያኔ መሪዎች ኢህአዴግ የሚባል አጋሰስ የሽፋን ድርጅት ፈጥረዉ በኢትዮጵያ ህዝብ ሰብዓዊ መብትና ነጻነትና ላይ ተነግሮም ተጽፎም የማያልቅ ግዙፍ ግፍና በደል ፈጽመዋል። ህጻን፤አዛዉንት፤ ወንድና ሴት ሳይለዩ መብቴን አትንኩ ያለቸዉን ኢትዮጵያዊ ሁሉ ያለምንም ርህራሄ በጥይት ጨፍጭፈዋል። ሴቶች እሀቶቻችንን እጅና እግራቸዉን አስረዉ ጡታቸዉን በመቆንጠጫ እየቆነጠጡ በሴትነታቸዉ ላይ የዉርደት ተግባር ፈጽመዋል። ወንዶች ወንድሞቻችንን ደግሞ ዉስጥ እግራቸዉን ገልብጠዉ እየገረፉ ጥፍራቸዉን አይናቸዉ እያየ በጉጠት እየሳቡ ነቅለዋል። ባጠቃላይ የወያኔ ዘረኞች በዛሬዉ ዘመን አንኳን ወገን በወገኑ ላይ የዉጭ ጠላትም በህዝብ ላይ የማይፈጽመዉ በደል በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ፍጽመዋል።
ወያኔ ስልጣን እንደያዘ “አባይ ትግራይ” ወይም “ታላቋ ትግራይ” የሚለዉን ህልሙን ለማሳካት ወልቃይት ጠገዴን ከጎንደር ቆርሶ ከትግራይ ጋር ቀላቅሏል። ስልጣን ይዞ ከተደላደለ ከአመታት በኋላ ደግሞ የኢትዮጵያን ገበሬ ከመሬቱ አፈናቅሎ ለምለም መሬቱን በርካሽ ዋጋ ለባዕዳን ሽጧል፤ ከዚህ አልፎ ተርፎም የአባቶቻችን አጽም ያረፈበትን የአገራችን ዳር ድንበር ቆርሶ ለጎረቤት አገር ገጸ በረከት አቅርቧል። ይህ አገራቸዉንና የሚመሩትን ህዝብ በሚጠሉ ጠባቦች የተሞላ ድርጀት ባለፈዉ ሳምንት የኢትዮጵያን ህዝብ ብቻ ሳይሆን ደጋፊዎቹንና በአንቀልባ ታዝለዉ አስከዛሬ ያቆዩትን ምዕራባዉያን ጭምር ግራ ያጋባ ፀረ አገርና ፀረ ህዝብ እርምጃ ወስዷል። ድርጅት እያፈረሰና በፓርቲ ላይ የራሱን ተለጣፊ ፓርቲ እያቋቋመ ዛሬ ላይ የደረሰዉ ወያኔ ምርጫ የሚባል ድራማ በደረሰ ቁጥር የሚይዘዉ በሽታ ዘንድሮም ይዞት አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲንና መላዉ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅትን አፍርሶ በምትካቸዉ የራሱን መኢአድና የራሱን አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ፈጥሯል። ይህ ወያኔ ከሰሞኑ የወሰደዉ የፖለቲካ እርምጃ በየትኛዉም አለም በተለይ የመድበለ ፓርቲ የፖለቲካ ስርዐትን እንከተላለን በሚሉ አገሮች ዉስጥ ታይቶም ተሰምቶም የማይታወቅ እጅግ በጣም ትልቅ የፖለቲካ ሸፍጥ ነዉ።
የወያኔን ታሪክ ተወልዶ ካደገበት ከደደቢት በረሃ እስከ ሚኒልክ ቤ/መንግስት ድረስ ያደረገዉን ጉዞ ስንመለከት ወለል ብሎ የሚታየን አንድ ሐቅ አለ፤ እሱም ወያኔ ሁሉንም ነገር በዘር መነጽር ብቻ የሚመለከትና ህዝብን በወዳጅና በጠላት ጎራ ለይቶ ወዳጅ አይደለም ያለዉን ሁሉ እንደ ሩሲያዊዉ ዮሴፍ ስታሊን እየገደለ የመጣ ድርጅት ነዉ። በእርግጥም ወያኔ ጫካ ዉስጥ እያለም ሆነ ዛሬ ከተማ ገብቶ የሚቃወመዉንና በሀሳብ የማይግባባዉን ድርጅትም ሆነ ግለሰብ እያፈረሰና እገደለ ባፈረሳቸዉ ድርጅቶች ምትክ ደግሞ የራሱን ተለጣፊ ድርጅት እየፈጠረ የመጣና ከዲሞክራሲያዊ አሠራርና ከስልጣኔ ጋር የማይተዋቅ ድርጅት ነዉ።
በመርፌ የተጠቃቀመ ቁምጣና ጥብቆ ለብሶ አስራ ሰባት አመት ጫካ ለጫካ የተጓዘዉ ወያኔ ጎንደር፤ ጎጃምና አምቦ እያለ ወደ አዲስ አበባ ሲጠጋ ከተገነዘባቸዉ ነገሮች አንዱ የለበሰዉ የተጠቃቀመ ቁምጣ የትም እንደማያደርሰዉና ለከተማ ኑሮ የሚስማማ አዲስ ልብስ እንደሚያሰፈልገዉ ማዉቁ ነዉ። በጥላቻ ተረግዞ በክፋት ላደገዉ ወያኔ ቢበቃዉም ባይበቃዉም ወይም ቢያምርበትም ባያምርበትም ይህንን ለከተማ ዉስጥ ኑሮ የሚያስፈልገዉን አዲስ ልብስ ለማዘጋጀት ብዙ ግዜ እልወሰደበትም። የሚሰርቅና የሚስቅ ምን ግዜም ተባባሪ አያጣም እንዲሉ ወያኔ የአዲስ አበባን መሬት የረገጠዉ ጦር ሜዳ ላይ የማረካቸዉን ወታደሮችና አገር ዉስጥ ያገኛቸዉን ደካማ ሰዎች ሰብስቦ በፈጠረዉ ኢህአዴግ በሚባል ፈረስ ጀርባ ላይ ተፈናጥጦ ነበር። ትግራይን ነጻ አወጣለሁ ብሎ ትግል የጀመረዉ ወያኔ ኢህአዴግን የፈጠረዉ ወያኔነቱን ለመተዉ ሳይሆን እራሱን በዚህ በኢትዮጵያ ስም በፈጠረዉ ድርጅት ዉስጥ ሸሽጎ እዉነተኛ ባህሪዩን ለመደበቅ ነበር።
ከግንቦት 1983 ዓም አስከ ግንቦት 1987 ዓም ድረስ የዘለቀዉንና በወያኔ የበላይነት ተጀምሮ ወያኔን በማንገስ የተጠናቀቀዉን የሽግግር መንግስት ወደ ኋላ መለስ ብሎ የቃኘ ማንም ሰዉ የወያኔን ሁለት ዋና ዋና መሠሪ ስራዎች በቀላሉ መመልከት ይችላል።
አንደኛ- ኦነግንና የደቡብ ህዝብ ንቅናቄን ጨምሮ አያሌ የፖለቲካ ፓርቲዎችንና ታዋቂ ግለሰቦችን አቅፎ ስራዉን የጀመረዉ የሽግግሩ መንግስት የስራ ዘመን የተገባደደዉ የኢትዮጵያን አንድነት ጥያቄ ያነሱ ግለሰቦችን በማሰርና ከወያኔ ቁጥጥር ዉጭ እራሳቸዉን ችለዉ ለመንቀሳቀስ የሞከሩ የፖለቲካ ድርጅቶችን ከሽግግሩ መንግስት በማባረር ነበር።
ሁለተኛ- ወያኔ የኋላ ኋላ እያደር ለመስራት ላቀዳቸዉ አገር የመበተንና ህዝብን የመለያየት ስራዎች እንዲያመቸዉ ከእያንዳንዱ የፖለቲካ ድርጅት ጀርባ የኢትዮጵያ ህዝብ ተለጣፊ እያለ የሚጠራቸዉን ድርጅቶች በራሱ አምሳል እየፈጠረ ማሰማራቱ ነዉ።
ባጠቃላይ ወያኔ የፈጠረዉ የሽግግር መንግስት ኢትዮጵያዊ አጀንዳና አገራዊ ራዕይ ይዘዉ የተንቀሳቀሱ ድርጅቶችንና ግለሰቦችን አጥፍቶ ወያኔን ዘለአለማዊ ንጉስ ለማደረግ ከመሞከሩ ዉጭ ሌላ ምንም ኢትዮጵያን የሚጠቅም ስራ አልሰራም።
ከሽግግሩ መንግስት በኋላ ወያኔ ተወዳዳሪዉም አሸናፊዉም እሱ ብቻ የሆነባቸዉን ሁለት ትርጉም የለሽ ምርጫዎችን አካሂዷል።እነዚህን ተወዳዳሪ የለለባቸዉን ሁለት ምርጫዎች በቀላሉ በማሸነፉ ህዝብ የወደደዉ መስሎት ልቡ ያበጠዉ ወያኔ ሦስተኛዉን አገራዊ ምርጫ ከመጀመሪያዎቹ ሁለት ምርጫዎች በተለየ መልኩ ለቀቅ አድርጎ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተወሰነ ደረጃም ቢሆን በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ፤ መራጩን ህዝብ መቅረብ እንዲችሉና ወያኔን እራሱን ምርጫዉን አስመልክቶ ክርክር እንዲገጥሙት በሩን ከፈተላቸዉ። ነገሩ “የማይነጋ መስሏት” እንዲሉ ሆነና ሜዳዉም ፈረሱም ይሄዉና ብሎ የፊልሚያዉን ሜዳ የከፈተዉ ወያኔ የምርጫዉ ቀን ደርሶ በዝረራ መሸነፉን ሲሰማ በራሱ ሜዳና በራሱ ዳኞች ፍት ያሸነፉትን የህዝብ ተመራጮች ከየመኖሪያ ቤታቸዉ እያደነ አስሮ በአገር ክህደት ወንጀል ከሰሳቸዉ ። የሚገርመዉ ወያኔ በምርጫዉ ተወዳድረዉ በምስክር ፊት በአደባባይ ያሸነፉትን የህዝብ ተመራጮች በማሰር ብቻ አልተወሰነም። በወቅቱ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደ አይኑ ብሌን ይመለከተዉ የነበረዉን ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲን አፍርሶ እንደለመደዉ የራሱን ቅንጅት ፓርቲ ፈጥሮ ይበጃል ብሎ ላሰባቸዉ ደካማና ሆዳም ግለሰቦች አስረክቧል።
ይህ ቆየት ያለ በሽታዉ ዘንድሮም አገርሽቶበት አንድነትንና መኢአድን ለክፏቸዋል። ይህ ወያኔ ከሰሞኑ መኢአድና አንድነት ላይ የወሰደዉ እርምጃ እነዚህ ሁለት ፓርቲዎች በመጪዉ ምርጫ ላይ ያሸንፉኛል ከሚል ፍራቻ አይደለም። ወያኔ ምርጫዉ የሚካሄድበት ሂደት ብቻ ሳይሆን ህዝብ የሰጠዉ ድምጽ የሚቆጠርበትና የምርጫዉ ዉጤት ለህዝብ የሚገለጽበት መንገድ ሙሉ በሙሉ በቁጥጥሩ ስር እንደሆነና ይህንን ምርጫ ብቻ ሳይሆን የሚቀጥለዉንም ምርጫ ከሱ ዉጭ ሌላ ማንም እንደማያሸንፍ በሚገባ ያዉቃል። ወያኔ መኢአድንና አንድነትን የጥቃቱ ሰለባ ያደረጋቸዉ ህዝባዊ አላማቸዉንና አገራዊ ራዕያቸዉን በተለይ እነዚህ ሁለት ፓርቲዎች በኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ፤ አንድነትና እኩልነት ጥያቄ ላይ ያላቸዉን የጠራና የማያወላዉል አቋም እጅግ በጣም ስሚጠላ ነዉ። ከዚህ በተጨማሪ ወያኔ እንዲህ በአጭር ግዜ ዉስጥ መኢአድንና አንድነትን የጨፈለቃቸዉ እነዚህ ሁለት አንጋፋ ፓርቲዎች አዲስ አበባን ጨምሮ በየክልሉ የዘረጉት መዋቅርና ከህዘብ ጋር የፈጠሩት የቅርብ ግኑኝነት እንቅልፍ ስለነሳዉ ነዉ። ሌላዉ በፍጹም መርሳት የሌለብን ነገር ቢኖር ይዋል ይደር እንጂ ወያኔ እኛ ቀድመን ካላጠፋነዉ በቀር “ኢትዮጵያዊነት” ፤ “አንድነት” ወይም ፍትህና ነጻነት ብሎ የተነሳን ማንንም ኢትዮጵያዊ ግለሰብ ወይም ድርጅት ማጥፋቱ አይቀርም። በእርግጥም ከትናንት ወዲያ ቅንጀትን፤ ዛሬ ደግሞ መኢአድንና አንድነትን አፍርሶ የራሱን ተለጣፊ አሻንጉሊቶች የፈጠረዉ ወያኔ ነገ እነዚህ ፓርቲዎች የቆሙለትን አላማ የተሸከምነዉን ኢትዮጵያዉያን አንድና ሁለት እያለ ለቃቅሞ እንደሚያጠፋን ምንም ጥርጥር የለዉም።
ወያኔ አምስት አመት አየቆየ በሚመጣዉ የምርጫ ድርማ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጀርባ ላይ እንደማይወርድ በ1997 ዓም ሰኔ ወርና በ 1998 ዓም ህዳር ወር በአዲስ አበባ አደባባዮች ላይ በወሰደዉ ፋሺስታዊ እርምጃ በግልጽ አሳይቶናል።ከላይ ከፍ ሲል ለመግለጽ አንደተሞከረዉ ወያኔ ፊታችን ላይ ባለዉ በ2007ቱ ምርጫ ወይም በተከታታይ በሚመጡት ምርጫዎች ተሸንፌ ከስልጣን እወርዳለሁ የሚል ምንም አይት ስጋት የለበትም፤ ምክንያቱም በምርጫዉ ጨዋታ ዉስጥ ተጫዋቹም ፤ ሜዳዉም ዳኛዉም ወያኔ ብቻ ነዉ። ዛሬ የወያኔን መሪዎች ያንቀጠቀጣቸዉና እንዳበደ ዉሻ ያገኙትን ሁሉ እንዲነክሱ ያደረጋቸዉ አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚኖረዉ ኢትዮጵያዊ በተግባራዊ ስራዎች ላይ መናበብ በመጀመሩና በህዝባዊ እምቢተኝነቱና በህዝባዊ አመጹ ዘርፍ የሚደረገዉ እንቅስቃሴ ህዝባዊ ሙቀት አግኝቶ እየተጋጋለ በመምጣቱ ነዉ። ወያኔዎች እነሱንና የገነቡትን ዘረኛ ስርዐት ከኢትዮጵያ ምድር ጠራርጎ የሚያጠፋዉ የህዝባዊ አመጹና የህዝባዊ እምቢተኝነቱ ጎርፍ መሆኑን ካወቁ ቆይተዋል። ይህ ከሰሞኑ በማሰር፤ በመደብደብና ድርጅት በማፍረስ የወሰዷቸዉ እርምጃዎች የሚያሳዩን ወያኔዎች ህዝባዊ ጎርፉን ቢቻል ለማጥፋት አለዚያም ጉዳት በማያደርስ መልኩ ለመገደብ ያሚያደርጉትን ከንቱ ሙከራ ነዉ።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፤ የኢትዮጵያ ወጣት፤ ገበሬና ሰራተኛ ባጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ ትናንት ቅንጅትን አፍርሶ የራሱን መናኛ ቅንጅት የፈጠረዉ ወያኔ ዛሬም እንደገና አሉ የሚባሉትንና አገራዊ ራዕይ ይዘዉ የሚንቀሳቀሱትን አንድነትንና መኢአድን አፍርሶ በምትካቸዉ እንደጌኛ ፈረስ የሚጋልብባቸዉን የራሱን ሁለት መናኛ ፓርቲዎች ፈጥሮ መኢአድና አንድነት ብሎ ሰይሟቸዋል። ይህ በዋና ዋናዎቹ ዘረኛ የወያኔ ባለስልጣኖች ተጠንቶ በጥንቃቄ የተወሰደዉ እርምጃ ፓርቲዎቹ ህግ ስላላከበሩ ነዉ የሚል ሽፋን ይሰጠዉ እንጂ የምርጫ ቦርዱ ሊ/መንበር ሳያስቡት ከአፋቸዉ አፈትልኮ የወጣዉ እዉነት በግልጽ እንዳስቀመጠዉ ከምርጫዉ ጨዋታ ወጥተዉ እንዲፈርሱ በተደረጉት አንድነትና መኢአድ ፓርቲና ወያኔ በተለጣፊነት ባስጠጋቸዉ ሁለቱ ተለጣፊ ፓርቲዎች መካከል ያለዉ ልዩነት አንዱ ቆሜለታለሁ ለሚለዉ ህዝብ የሚታዘዝ ህዝባዊ ሌላዉ ደግሞ ሆዱን ለሚሞላለት ወያኔ የሚታዘዝ ሆዳም መሆናቸዉ ብቻ ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ ወያኔ መብቴን ብለህ ስትጮህ በጥይት እየጨፈጨፈህ ነጻነት ስትለዉ በዱላ እየደበደበህና ሰላማዊ ሰልፍ ስትወጣ ደግሞ አፍሶ እያሰረህና ዉስጥ እግርህን ገልብጦ እየገረፈህ በሰላማዊ መንገድ የምታደርገዉን ትግል ምርጫ አሳጥቶሃል። ሆኖም ግልጽ በሆነ መንገድ እንነጋገር ከተባለ ወያኔ የትግል አማራጭ አያሳጣህም፤ ሊያሳጣህም አይችልም። ወያኔ እሱ እራሱ ህግ በሆነበት አገር ህጋዊ ወይም ሠላማዊ ትግል ብሎ ነገር ዋጋ ቢስ አንደሆነ ሁላችንም የተረዳን ይመስላል። ትግላችን ህዝባዊ እምቢተኝነት ነዉና ከዛሬ በኋላ ወያኔን ጥያቄ አንጠይቀዉም፤ አድርጉ የሚለንን አናደርግም፤ ሁኑ የሚለንንም አንሆንም። ትግላችን ህዝባዊ አመጽ ነዉና ከዛሬ በኋላ ወያኔ ሲገድለን እኛም እየገደልነዉ እንሞታለን እንጂ አንገታችንን ደፍተን የእሳት እራት አንሆንም። አዎ! ት ግላችን እምቢ ማለት ወይም ህዝባዊ እምቢተኝነት ነዉ፤ ትግላችን በወያኔ ላይ ማመጽ ወይም ህዝባዊ አመጽ ነዉ።

mandag 2. februar 2015

ወያኔ የጋረደብንን የመበታተን አደጋ ለማክሸፍ ትግላችንን ማቀናጀትና በአንድ የአመራር ጥላ ሥር ማሰባሰብ ወቅቱ የሚጠይቀን እርምጃ ነው

February 2,2015
ትግራይን ከተቀረው የአገራችን ክፍል ለመገንጠልና የትግራይን ሪፑፕልክ ለማቋቋም ራዕይና ተልዕኮ ሰንቆ የዛሬ 40 አመት ደደቢት በረሃ ውስጥ የተፈጠረው ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ፡ በለስ ቀንቶት የመንግሥት ሥልጣን ከተቆጣጠረ ወዲህ፡ በስሙ የሚነግድበትን የትግራይን ህዝብ ጨምሮ በአገራችንና በመላው ህዝባችን ላይ የፈጸማቸው ወንጀሎችና ያደረሳቸው ሰቆቃዎች ተዘርዝረው የሚያልቁ አይደሉም::
ከነዚህ ወንጀሎች ሁሉ የከፋውና ምናልባትም የሚቀጥለውን ትውልድ ጭምር ዋጋ ያስከፍላል ተብሎ የሚፈራው ምዕራባዊያን ቅኝ ገዥዎች አህጉራችን አፍሪካን በተቀራመቱበት ወቅት የአገዛዝ ዘመናቸውን ለማራዘምና ቅኝ የገዙዋቸውን ህዝቦች ሃብትና ንብረት ለመዝረፍ እንዲመቻቸው የተጠቀሙበትን የከፋፍለህ ግዛ ፖሊስ በምድራችን ተግባራዊ በማድረግ ለዘመናት የተገነባውን የህዝብ አንድነትና የአገር ሉአላዊነት ሊያናጋ በሚችል መልኩ በዘር፤ በቋንቋና በሃይማኖት ተከፋፍለን የጎሪጥ እንድንተያይ የተፈጸመብን ደባ ነው::
በዚህ ደባ ምክንያት ዛሬ በአገራችን ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሆኔታ ኦሮሞነት፤ ሱማሌነት፤ ትግሬነት፤ አማራነት ፤ ስዳማነት፤ አፋርነት፤ ወላይታነት ፤ ከምባታነት ወዘተ ከዘግነት በላይ ገዝፎ የማንነት መለያና የፖለቲካ፤ የኢኮኖሚና ማህበራዊ መብቶች መሠረት ሆኖአል:: በዚህም የተነሳ የኦሮሞ ከብት አርቢ ለከብቶቹ ግጦሽ ፍለጋ ወደ ሱማሌ ድንበር ከተሻገረ እንደ ባዕድ ተቆጥሮ ተኩስ ይከፈትበታል፤ አፋር ወደ ኢሳ ከተሻገረ ይገደላል፤ ለቤነሻንጉል በተከለለ ክልል የሰፈረ የአማራ አርሶ አደር የደከመበትን አንጡራ ሃብት ተቀምቶ ይባረራል፤ አኝዋክ ለዘመናት ተከባብሮና ተቻችሎ ከኖረው ከኑዌር ወንድሙ ጋር እንዲጋጭ ተደርጎ በገላጋይነት ሥም የፈደራል ፖልስና የጸጥታ ሃይል በጅምላ እንዲጨፈጭፈው ይፈረድበታል :: በመልካም አስተዳደር እጦት የደረሰበትን መከራና ስቃይ አብሮ ሲጋፈጥ የኖረው የወልቃይት ጠገደ ህዝብ አንተ አማራ አንተ ትግሬ በሚል የዘር ክፍፍል ለመገዳደል ካራውን ስሎ ተቀምጦአል :: ይህ አልበቃ ብሎም የአንድ ብሄር አባላትን በጎሳ ሸንሽኖ የጉጂ ኦሮሞ ከአርስ ወንድሙ ጋር ደም እንዲቃባ ተደርጎአል:: የኦጋዴን የተለያዩ ጎሳዎችም ላይ እንዲሁ::
ወያኔ በጉልበት የጫነብን የመከፋፈልና የመለያየት አደጋ አንድ ቀን ሲያበቃ የነጻነት ብርሃን ፈንጥቆ በሠላምና በመቻቻል የምንኖርበት አገር እንኳ እንዳይኖረን በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች መጠነ ሰፊ የሆነ ድንግል መሬታችንን ለህንድ፤ ለቻይናና ለአረብ ከበርቴዎች በርካሽ ዋጋ በመቸብቸብ በገዛ አገራችን የባዕዳን አሽከሮች ሆነን እስከ ዘለአለሙ እንድንኖር መሠረት ተጥሎአል::
ይህ ሁሉ በደልና መከራ እንዲያበቃ በአገዛዙ ላይ የተቃውሞ ድምጹን ያሰማ ከሥራውና ከኑሮው ተፈናቅሎ በድህነት አረንቋ ውስጥ እንዲጣል አለያም እየታደነና የሽብርተኝነት ታፔላ እየተለጠፈበት ወደ የማጎሪያ ጥቢያዎች እንዲወረወር ተደርጎአል:: በዘርና በቋንቋ በተከለለልን ክልል በፈረቃ የሚደርስብንን አፈናና ሰቆቃ በህብረት ለመቃወም የሚደረጉ ጥረቶች በሙሉ “የቀድሞ ሥርዓት ናፋቂ፤ ትምክህተኛ ፤ አክራሪ/ጽንፈኛ፤ ጸረ ልማት ወዘተ ” በሚሉ የማሸማቀቂያና የመወንጀያ ቃላቶች ጋጋታ እንዲደናቀፍ ለማድረግ ተሞክሮአል::
ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄና የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ጥር 2 ቀን 2007 አመተ ምህረት የፈጸሙት ውህደት ዋናው ምክንያት ከላይ የተዘረዘሩትን ግፎች ለማስቆም በተናጠል ከሚደረግ ትግል በህብረት የሚደረገው ትግል ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑ የፈጠረው ግንዛቤ ነው :: የወያኔ የጥቃት ክንዶች የፈረጠሙት በራሱ ጥንካሬ ወይም የሚተማመንበት ህዝባዊ ድጋፍ በደጀንነት ኖሮት ሳይሆን በኛ መከፋፈልና መለያየት ብቻ እንደሆነ ህዝባችን ከተረዳው ውሎ አድሮአል::
አርበኞች ግንቦት 7 በሚል መጠሪያ ሁለቱ ድርጅቶች በቅርቡ የፈጠሩት ውህደት ከድህረ ምርጫ 97 ጀምሮ ህዝባችን ከደረሰበት ስቆቃ ለመገላገል ተቃዋሚዎችን “ተባበሩ ወይም ተሰባበሩ” በማለት ሲያቀርብ ለኖረው የድረሱልኝ ጥሪ የተሰጠ የመጀመሪያው ተግባራዊ ምላሽ ነው:: ሁለቱም ድርጅቶች እስከ ዛሬ ምድር ላይ ያደራጁትን የሰው ሃይል ፤ እውቀትና ንብረት አዋህደው በአንድ አመራር ሥር ትግሉን ከዳር ለማድረስ መወሰናቸው በአላማና ግብ ለሚመሰሉዋቸው ሌሎች ተቃዋሚ ሃይሎች ብቻ ሳይሆን ወያኔን ከህዝብ ጫንቃ ላይ በማውረድ ፍትህና እኩልነት በአገራችን እንዲሰፍን እንታገላለን ለሚሉት ሃይሎች ሁሉ አርአያነት ያለው እርምጃ መሆኑ እየተነገረ ነው :: የአርበኞች ግንቦት 7 ውህደት በተፈጸመበት ሥነሥርዓት ላይ አገራቸውን ነጻ ለማውጣት ነፍጥ አንግበው ከሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች ውስጥ የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ [ዴሚት] ሊቀመንበር አቶ ሞላ አስግዶም ፡ የአፋር ነጻነት ግንባር [አርዱፍ] ሊቀመንበር አቶ ኢብራሂም ሙሳ ፤የጋምቤላ ህዝብ ነጻነት ንቅናቄ [ጋህነን] ሊቀመንበር አቶ ኦኬሎ አይዴድ ፡ የቤነሻንጉል ተወካይና የአድሃን ተወካዮች በየተራ የተናገሩት በአንድ የጋራ ግንባር ሥር ተሰባስቦ በገንዘብና በመሣሪያ ብዛት ተብቶ የህዝባችንን መከራና ስቃይ እድሜ እያራዘመ ያለውን የጥቂቶች አገዛዝ በሃይል የማንበርከክ አስፈላግነትና ወቅታዊነት ሁለቱ ድርጅቶች የፈጸሙት ውህደት ለትብብር ፈር ቀዳጅ መሆኑን አመላክቶአል :: አገራችንን ከመበታተን አደጋ ለመታደግ ወያኔ ባወጣቸው የአፈና ህጎች ተገዝተን ለውጥ ማምጣት አንችልም ያልን ሃይሎች እየተዋሃድንና እየተጣመርን በሄዱን ቁጥር አፈናና እንግልት ተቋቁመን እንታገላለን ያሉት ሃይሎችም በተናጠል ከሚደርስባቸው ጥቃት ለመገላገል ሲሉ ወደ ውህደትና ጥምረት ጎዳና ማቅናታቸው የማይቀር ነው::
ህዝባችን ላይ የደረሰው ግፍና መከራ ጻዋ ሞልቶ እየፈሰሰ ባለበት በዚህን ሰዓት የአገሩ ጉዳይ አሳስቦት በፖለቲካ ድርጅቶች ዙሪያ የተሰባሰበ ወገን ሁሉ ለመቀራረብና ለመተባበር እያደረገ ያለው ጥረት ተስፋ ሰጪና አበረታች ሆኖአል:: በዚህ አጋጣሚ ላለፉት 24 አመታት ወያኔ በወገኖቻችን ላይ ለፈጸማቸው ሰቆቃዎች በመሣሪያነት ያገለገሉና እያገለገሉ ያሉ ወገኖች በሙሉ ከውህዱ አርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አንድ የተላለፈላቸው ወገናዊ ጥሪ አለ:: ይህም ጥሪ እስከ ዛሬ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ወይም ለሥራ ዋስትና ብላችሁ የዚህ ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ መሳሪያ በመሆን በወገኖቻችሁ ላይ ግዲያ ፤ እስርና ግርፋት ስትፈጽሙ የኖራችሁ ሁሉ የበደላችሁትን ህዝብ ለመካስ የአገዛዙን ዕድሜ ለማሳጠር በምናደርገው የሞት ሽረት ትግል ላይ እንቅፋት ከመሆን እራሳችሁን አግልሉ ! የሚል ነው:: ትግላችን ወሳኝ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ገና ከመድረሱ ከህዝብ በዘረፉት ሃብትና ገንዘብ ልጆቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ወደ ባህር ማዶ ማሸሽ ለጀመሩት ስግብግብ አለቆችህ ምቾትና ድሎት ብለህ ይህ የመከራ ዘመን ሲያልፍ በሃላፊነት የሚያስጠይቅህን ወንጀል ለነጻነት በሚታገሉ ወገኖችህ ላይ እንዳትፈጽም ለአገር የመከላኪያ ሠራዊት፤ ለፖልስና የጸጥታ ሃይል አባላት ሁሉ ጥሪ ቀርቦአል::
የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በቀር ድል ማድረጋችንን ፈጽሞ የማንጠራጠር የነጻነት ታጋዮች በሙሉልብ የምንናገረው ወያኔ አገራችንን ለመበታተን የቻለውን ሁሉ ድንጋይ ቢፈነቅልም በአንድ የአመራር ጥላ ሥር ተሰባስበን አገራችንን ከተጋረጠባት የመበታተን አደጋ ለመታደግና እያንዳንዱ ዜጋ የሚኮራባት የበለጸገችና ሉአላዊነቷ የተረጋገጠ አገር ባለቤት ለመሆን የጀመርነው ትግል ግቡን እንደሚመታ ነው:: ለዚህ ደግሞ በቅርቡ የፈጸምነው ውህደትና ከሌሎች ጋር በጥምረት ጠላትን ለመፋለም የጀመርነው ተግባራዊ እንቅስቃሴ ወቅታዊነት ለወገን ተስፋ ለጠላት መርዶ ነው::
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !