søndag 4. oktober 2015

ኢሳት በእኛ ድጋፍ ይቀጥላል!!


ኦክቶበር 2, 2015
ዲቦራ ለማ/ኖርዌ/

አለማችን አሁን ያለችበት ዘመን በከፍተኛ  ደረጃ መረጃ ከአንዱ ወደ አንዱ በየሰከንዱ እየፈሰሰ አለምን ወደ አንድ ጎራ አምጥቶ የመረጃን ጠቃሚነት እያየን የመጣንበት ጊዜ ነው። መረጃ የአንድን ሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፓለቲካዊ እንቅስቃሴን ለማዳበር ከፍተኛውን ሚና ይጫወታል።

እንደሀገራችን ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት ደግሞ በተቃራኒው መረጃ ለህዝብ እንዳይደርስ የመረጃ መረቦችን በሙሉ በመበጣጠስና በማገድ ትክክለኛ መረጃ ለህዝብ እንዳይደርስ ሲከላከሉ እናያለን። በሀገራችን ኢትዮጵያ ያለው የመረጃ ምንጭ አንድ የገዥው ፓርቲ ልሳን የሆነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዝንና ራዲዮ ሲሆን ሌሎችም የስርአቱ አቀንቃኝ የሆኑ እንደ ሬዲዮ ፋና ያሉ የግል ልሳናት አሉ። እነኚህ የወያኔ ልሳኖች አርባ ስምን ሰአት ያለምንም እፍረት የስርአቱን ፕሮፓጋንዳ ሲያሰራጩ ውለው ያድራሉ።
ህዝቡ ትክክለኛ መረጃ እንዳያገኝ ከፍተኛ ጫና በማሳደርና የህዝቡን ንብረት በመዝረፍና ህዝቡን ጦም በማሳደር በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር በመክፈል ትክክለኛ መረጃ እያቀረበልን የሚገኘውን የኢሳትን ጣቢያ በተደጋጋሚ በማፈን ስርጭቱን ለማቋረጥ ወያኔ ብዙ ሙከራ ሲያደርግ መቆየቱ ይታወቃል።

ሆኖም ግን ኢሳት በህዝብ ድጋፍ ዛሬም ትክክለኛ መረጃን እያደረሰ የህዝብ አይንና ጆሮ ሆኖ ቀጥሏል። አምባገነኑ የወያኔ ስርአት ትክክለኛ መረጃን ለህዝብ የሚያቀርቡ ጋዜጠኞችንና ፀሀፊዎችን በእስር በማንገላታትና ከሀገር በማሰደድ መረጃን ሊያጠፋ ቢሞክርም ኢሳት ግን ዛሬም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ጨምሮ በሀገሪቱ ላይ የሚሰሩ ወንጀሎችን በማጋለጥ ለህዝቡ መረጃን እያቀረበ ይገኛል።

ኢሳት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ተደማጭነት ያለውና አንድ ብቸኛ ትክክለኛ መረጃ አቅራቢ ተቋም ሆኖ በህዝብ ድጋፍ የሚንቀሳቀስ የህዝብ ሀብት ነው። ኢሳት በዚህ መልኩ በብዙ መሰናክሎች ውስጥ አልፎ  እነሆ ዛሬ 5ተኛ አመቱን በተለያዩ ሀገራት እያከበረ ይገኛል። በኦክቶበር  24, 2015 ደግሞ የኖርዌ ዋና ከተማ በሆነችው ኦስሎ ኢሳት 5ተኛ አመቱን በከፍተኛ ሁኔታ ለማክበር በዝግጅት ላይ ይገኛል። በመሆኑም በኖርዌ በተለያዩ ከተሞች የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ወደዚህ ዝግጅት ተጋብዛችኋል።

የአምባገነኖችን እድሜ ለማሳጠርና ዲሞክራሲያዊ መንግስት ለመመስረት ትክክለኛ መረጃ ለሀገራችን ህዝብ ወሳኝ በመሆኑ ኢሳት እንዲቀጥል የሁላችንም ተሳትፎ አስፈላጊ በመሆኑ በስፍራው ተገኝተን የበኩላችንን አስተዋፅኦ እናድርግ ብዬ ጥሪዬን አቀርባለሁ።



መረጃ ኃይል ነው


በእኛ ድጋፍ ኢሳት ይቀጥላል!!!!

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar